
ባሕር ዳር: ጥቅምት 18/2018 ዓ.ም (አሚኮ) 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) በተገኙበት 2ኛ መደበኛ ስብሰባውን እያካሄደ ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለተነሱ ጥያቄዎች ማብራሪያ እየሰጡ ይገኛሉ።
በማብራሪያቸውም ኢንዱስትሪ ባለፈው ዓመት 13 በመቶ ማደጉን ገልጸዋል። የኢንዱስትሪ እድገቱ የሚጨበጥ ለውጥ እያመጣ መኾኑንም ተናግረዋል። የባለፈው ዓመት የነበረው እድገት ጥሩ ነበር ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዘንድሮው እድገታችን ደግሞ ደብል ድጂት እናድጋለን ነው ያሉት።
ለውጡ የኢትዮጵያን የፋይናንስ ዘርፍ ከሞት የታደገ መኾኑን ገልጸዋል። ባለፈው ዓመት መንግሥት ከብሔራዊ ባንክ ሳይበደር ኢኮኖሚውን መምራቱን ተናግረዋል። “ለውጡ ከታሰበው እና ከታለመው ባሻገር የተሳካ ነው” ብለዋል።
የዓለም ባንክ የኢትዮጵያ እድገት መጨመሩን በተደጋጋሚ እየተናገረ መኾኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ መገኘቱንም አንስተዋል። የኢትዮጵያን እድገት ጥሩ አፍንጫ፣ ዓይን እና ጀሮ ያለው የሚገነዘበው ነው ብለዋል። ነገር ግን የኢትዮጵያ እድገት አልቋል ማለት አይደለም ነው ያሉት።
የዋጋ ግሽበትን ለመቆጣጠር ሥራ መሠራቱንም ገልጸዋል። የዋጋ ግሽበትን ለመቆጣጠር በተሠራው ሥራ ረግቧል ነው ያሉት። የተገኘውን ውጤት አስቀጥለን፣ ክፍተቶችን እየሞላን ከሄድን የኢትዮጵያን ብልጽግና እናረጋግጣለን ነው ያሉት።
ዘጋቢ:- ታርቆ ክንዴ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
