
ባሕር ዳር: ጥቅምት 18/2018 ዓ.ም (አሚኮ) 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 2ኛ መደበኛ ጉባኤ እየተካሄደ ይገኛል።
በዚህም የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽ እና ማብራሪያ እየሰጡ ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በ2017 በጀት ዓመት የማይሳኩ የሚመስሉ ፕሮጀክቶች በመሳካታቸው እንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል።
ከግብርና መር የኢኮኖሚ ፖሊሲ ወደ ብዝኀ ዘርፍ እና ተዋናይ የኢኮኖሚ አቅጣጫ መከተል እንደሚገባም ገልጸዋል። ሽግግሩም ውጤታማ እየኾነ ነው ብለዋል።
ግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝም እና ቴክኖሎጂ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ከሌሎች ጋር ተጣምረው እንዲመሩ ይደረጋል ነው ያሉት።
በዚህ አቅጣጫም የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ለውጥ እያመጣ መኾኑን ገልጸዋል።
መንግሥት ከግሉ ሴክተር፣ ከሕዝብ እና ከአጋር ድርጅቶች ጋር ተባብሮ የኢትዮጵያን ልማት ያፋጥናል ነው ያሉት።
ከለውጡ በኋላ ለፐብሊክ ፓርትነር ሺፕ ትኩረት መሰጠቱንም አንስተዋል። 48 ቢሊዮን ችግኝ የተተከለውም በዚሁ ስልት 25 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን የተሳተፉበት መኾኑንም አመላክተዋል። ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
ከሪፎርሙ ዋና ዓላማዎች ውስጥ የማክሮ ኢኮኖሚ መዛባትን እና እዳን ማረቅ፣ የንግድ እና ኢንቨስትመንት ከባቢን ምቹ ማድረግ፣ የዘርፍ ምርታማነትን እና ተወዳዳሪነትን ማሳደግ፣ የማስፈጸም አቅምን ማሳደግ፣ ዘላቂ የፋይናንስ ሥርዓት እና የጥራት ዕድገት ማረጋገጥ፣ እና ሌሎች ዓላማዎችን ማረጋገጥ ነበር ብለዋል።
ተግባሩም ገቢን በማሻሻል ለውጥ መምጣቱን፣ ኤክስፖርት መሻሻሉን፣ እዳ ለማሸጋሸግ ድርድር ተደርጎ ከ4 እስከ 4 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር ሽግሽግ በመደረጉ ኢትዮጵያ እዳዋን ለመክፈል ችግር እንደሌለባት፣ የኢትዮጵያ እዳ ሳይስተካከል ከለውጡ በኋላ የንግድ ብድር አለመወሰዱን እና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት መሻሻሉን ዘርዝረዋል።
ከለውጡ ወዲህ በሁሉም መስፈርት ሲታይ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ስብራቶች መጠገናቸው እና ውጤታማ መኾናቸውንም አንስተዋል።
በዋሴ ባየ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
