“ኢትዮጵያ በተጠናቀቀዉ በጀት ዓመት በርካታ እመርታዊ ለውጦችን አስመዝግባለች” የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት

4
ባሕር ዳር: ጳጉሜን 03/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት ጳጉሜን ሦሥት የእምርታ ቀንን ምክንያት በማድረግ መልዕክት አስተላልፏል።
እመርታ ለዘላቂ ከፍታ!
እንኳን ጳጉሜን ሦሥ የእመርታ ቀን አደረሳችሁ። የእመርታ ቀንን የምናከብረዉ የጀመርነዉን የከፍታ ጉዞ በማላቅ እና በማጽናት የኢትዮጵያን ብልጽግና ለማረጋገጥ ነው፡፡
ኢትዮጵያ በተጠናቀቀዉ በጀት ዓመት በርካታ እመርታዊ ለውጦችን አስመዝግባለች፡፡ ወደተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ትግበራ ውስጥ ገብታ ያለመችዉን አሳክታለች፡፡ የተረጋጋ ማክሮ-ኢኮኖሚ መፍጠር፣ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ፣ የኢንዱስትሪ ምርቶችን ተወዳዳሪነትና የገበያ ድርሻ ማሳደግ፣ የማዕድን ዘርፉን ዐቅም እና ሕጋዊ ሥርዐት ማጠናከር፣ የቱሪዝሙን የኢኮኖሚ ድርሻ ማላቅ፣ ዲጀታላይዜሽንን ማስፋፋት እና የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥን ማዘመን በማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ትግበራዉ ትኩረት የተሰጣቸዉ ነበሩ፡፡
በመኸር፣ በበጋ መስኖ፣ በሌማት ትሩፋት እና በአረንዴ ዐሻራ በልዩ ትኩረት የተሠራበት ግብርና እመርታዊ ስኬት ተመዝግቦበታል፡፡
ለማክሮ ኢኮኖሚዉ መረጋጋት ከመፍጠሩም ባሻገር ለዓለማቀፍ ገበያ ምርቶች ቀርበዋል፡፡ ቡና፣ ማንጎ፣ የቅባት እህሎች እና ሌሎችም ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ቡናን ብቻ ብንወስድ በታሪኩ ከፍተኛዉን የውጭ ምንዛሬ ያስገኘበት ዓመት ነበር፡፡ በሥጋ እና እንቁላል አቅርቦትም ከፍተኛ መሻሻል ታይቷል፡፡
የኢንዱስተሪዎች የማምረት ዐቅም በእጅጉ ተሻሽሏል፡፡ ተኪ ምርቶችን በከፍተኛ መጠን እያመረቱ ነው፡፡ በዓለማቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እና ተፈላጊ ምርቶችን በማምረትም ኤክስፖርት እያደረጉ በመቶ ሚሊዮኖች ዶላር ማስገባት ጀምረዋል፡፡ የከተሞች መሠረተ ልማቶች እየዘመኑ መምጣት፣ እንደ ኅዳሴ ያሉ ግዙፍ የኃይል አቅራቢ ግንባታዎች መጠናቀቅ፣ የጥራት መንደርን መሰል ተቋማት መገንባት ደግሞ በቀጣይ ኢንዱስትሪዉን ብቁ እና ተወዳዳሪ ለማድረግ ጥልቅ መሠረት የጣሉ ናቸው፡፡
ኢትዮጵያ በአሏት የማዕድንና የመስሕብ ጸጋዎች ልክ እንድትጠቀም ሰፊ ሥራ ተሠርቷል፡፡ የወርቅ ማውጣት ሥራዉንና ግብይቱን በከፍተኛ ደረጃ በማሻሻል እጅን በአፍ የሚያስጭን ስኬት ተመዝግቧል፡፡ ከዚህ ቀደም በዓመት ይገኝ ከነበረዉ በብዙ እጥፍ ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ቀርቧል፡፡ የቱሪዝም መዳረሻዎች በእጅጉ ተስፋፍተዋል፤ ለጎብኝዎች ምቹ ተደርገዋል፡፡ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ባልተለመደ መልኩ አድጎ በዓመቱ ከ150 ያላነሱ ዓለማቀፍ ጉባኤዎች ተመዝግበዋል፡፡
እነዚህ ስኬቶች ኢትዮጵያ ያለመችውን ለማሳካትና ለማንሰራራት መሠረት መጣል ያስቻሉዋት አስደማሚ ስኬቶች ናቸው፡፡ ታሪክ ቀያሪ አመርታዎች ናቸው፡፡ በመሆኑም የተጀመሩ እመርታዊ ስኬቶችን አጠናክሮ ለመቀጠልና የኢትዮጵያን ርዕይ ወደሚጨበጥ ብርሃን ለማሸጋገር ጳጉሜን ሦሥት የእመርታ ቀን ተብሎ ተሰይሞ እመርታ ለዘላቂ ከፍታ በሚል መሪ ቃል በተለያዩ ኹነቶች በመከበር ላይ ይገኛል፡፡
መልካም የእመርታ ቀን እንመኛለን!
ጳጉሜን 3/2017 ዓ.ም
የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን
Previous articleየኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የግብጽ ደጋፊዎች በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ላይ ላሳዩት ያልተገባ ባሕሪ እርምት እንዲወስድ ለፊፋ ጥያቄ አቀረበ።
Next articleየተሠሩ የመሠረተ ልማት ሥራዎች መሠረታዊ እና ችግር ፈች ናቸው።