
ባሕር ዳር: ነሐሴ 3/2016 ዓ.ም (አሚኮ)በገቢዎች ሚኒስቴር የመካከለኛ ግብር ከፋዮች ወይይት እየተካሄደ ነው። በውይይቱ ላይ የገቢዎች ሚኒስተር ዓይናለም ንጉሴ፣ የገንዘብ ሚኒስትሩ አሕመድ ሽዴ እና የጉምሩክ ካሚሽነር ደበሌ ቀበታ ተገኝተዋል። የገቢዎች ሚኒስትር ዓይናለም ንጉሴ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤታቸው ለልማት የሚያስፈልግውን ገቢ በመሰብሰብ ደረጃ ከፍተኛ መሻሻል እያሳየ ስለመኾኑ ተናግረዋል።
ነገር ግን ገቢን መሰብሰብ በሚፈለገው ደረጃ እንዳልተደረሰ በመግለጽ በቀጣይም የተሻለ ገቢ መስብስብ እንዲቻል ውይይቱ አስፈላጊ መኾኑን ተናግረዋል። የ2017 በጀት ዓመትን ስኬታማ ለማድረግ ግብርን በፈቃደኝነት መክፈል፣ ዲጅታል የታክስ አስባስብ ሥርዓትን ማጠናከር፣ የታክስ ፍትሐዊነትን ማስፈን፣ ከአጋር እካላት ጋር በትብብር መሥራት እንዲሁም የዳበረ የሥራ ባሕል መፍጠር ላይ ትኩረት ተደርጎ እንደሚሠራ ገልጸዋል።
የገንዘብ ሚኒስትሩ አሕመድ ሽዴ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውን በሁሉም ዘርፎች ላይ በመተግበር የሀገራችን ወጪ በሀገራችን ገቢ መሸፈን የትኩረት መስክ እንደኾነ ጠቁመዋል። የኢኮኖሚ ሪፎርሙ የገሪቷን ምጣኔ ሃብታዊ እንቅስቃሴ የሕግ የበላይነት የሰፈነበት፣ ዘመናዊ፣ ተወዳዳሪ፣ ምርታማነቱ የጨመረ እና ከእዳ ጫና የተላቀቀ የሚያደርገው መኾኑን ገልጸዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!