በገዳሪፍ ክፍለ ግዛት ዋና አስተዳዳሪ ሜጀር ጀኔራል ነስረዲን አብዲ የተመራ ልዑክ ጎንደር ገባ።

163

ልዑኩ ጎንደር ከተማ ሲደርስ የከተማዋ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ኢንጅነር ማስተዋል ስዩምና ሌሎች የሥራ ኃላፊዎች አቀባበል አድርገውለታል።

የገዳሪፍ ክፍለ ግዛት ዋና አስተዳዳሪ እና ልዑካቸው ነገ ቅዳሜ የካቲት 7/2012 ዓ.ም የወረታ ደረቅ ወደብና ተርሚናል ምረቃ መርሀ ግብር ላይ እንደሚታደሙ ይጠበቃል።

በመርሀ ግብሩ የአማራ ክልል ርዕሰ መሥተዳድር ተመሥገን ጥሩነህ፣ የክልሉና የፌዴራል የሥራ ኃላፊዎች እንደሚገኙ ነው የሚጠበቀው።

ነገ ከሰዓት እና እሁድ ደግሞ የአማራ ክልል የሥራ ኃላፊዎች እና የገዳሪፍ ክፍለ ግዛት ልዑክ የጋራ ጉዳዮቻቸው ላይ በባሕር ዳር ይመክራሉ፤ መሠረተ ልማቶችንም ይጎበኛሉ።

ኢትዮጵያ በአማራ ክልል በኩል፣ ሱዳን ደግሞ በገዳሪፍ ክፍለ ግዛት ሰፊ ወሰን ይጋራሉ። የአማራ ክልል እና የገዳሪፍ መሪዎችም በድንበር አካባቢ ፀጥታን ለማስከበር፣ የኮንትሮባንድ ንግድን ለመቆጣጠር እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች በጋራ ለመሥራት በየጊዜው እየተገናኙ እንደሚመክሩ ይታወቃል።

ዘጋቢ፦ ፍጹምያለምብርሃን ገብሩ

Previous articleየሀገራቱ አቋምም ሆነ የሌሎች ተጽእኖ ብሔራዊ ጥቅምን አሳልፎ የሚሰጥ ድርድር ውስጥ እንደማያስገባ ሚኒስቴሩ አስታወቀ፡፡
Next articleከ100 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ የተደረገበት የወረታ ደረቅ ወደብ እና ‹ተርሚናል› ግንባታ ተመረቀ።