
ባሕር ዳር፡ ነሐሴ 12/2013 ዓ.ም (አሚኮ) ጋዜጠኛና ጸሐፊ ጄፍ ፒርስ በማይካድራ የተፈጸመውን አሰቃቂ ጭፍጨፋ እውነታውን ለማወቅ በሚል በስፍራው በመገኘት ዘገባ ሠርቷል።
ጄፍ ፒርስ በማይካድራ በንጹሐን ላይ የተፈጸመውን አሰቃቂ ጅምላ ጭፍጨፋ ታላላቆቹ የዓለም የሚዲያ አውታሮች ሽፋን ሊሰጡት እንዳልፈለጉ ተናግሯል።
በማይካድራ ተጎጂዎችን በማነጋገር ባዘጋጀው ዘገባ እንደተመለከተው ሳምሪ የተባሉ የአሸባሪው ህወሓት ቡድን አባላት አማራዎችን ብቻ በመምረጥ በጦር መሳሪያ፣ በገጀራ፣ በጩቤና በፋስ ተጠቅመው መጨፍጨፋቸውን ገልጿል።

አካባቢው በርካታ ሠርቶ አዳሪ ዜጎች መኖሪያ በመሆኑ ለሥራ የሄዱ ወጣቶች ሰብሰብ ብለው በአንድ ቤት ማደራቸው የተለመደ መሆኑ ጉዳቱን ከፍ እንዳደረገው በምርመራው ላይ የተሳተፉ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎችን ዋቢ በማድረግ ያብራራው ጄፍ ፒርስ፤ ጭፍጨፋው በአሸባሪው ቡድን አባላትና ሳምሪ በተባለ ገዳይ ቡድን ቅንጅት የተፈጸመ መሆኑን ገልጿል።
የጭፍጨፋው ፈጻሚዎች ማንነት በተጎጂዎቹ በሚገባ ታውቀው እያለ ዓለማቀፉ ማኅበረሰብ ምንም አለማለቱ አስገራሚ ብቻም ሳይሆን አሳዛኝ መሆኑን እንደገለፀ ኢዜአ ዘግቧል።

ጄፍ ፒርስ በሩዋንዳ የተፈጸመው አሳዛኝ ድርጊት ከአስርት ዓመታት በኋላ በኢትዮጵያም መከሰቱ የብዙዎችን ልብ የሰበረ መሆኑን ተናግሯል።
ከ50 እስከ 60 የሚሆኑ ሰዎች በአንድ ጉድጓድ ስለመቀበራቸው የተናገረው ጸሐፊው ጭፍጨፋው ታስቦና ታቅዶ በቅንጅት የተፈጸመና ድርጊቱም የከፋ መሆኑን አስረድቷል።

ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ