
በጀርመን ሙኒክ ለታላቁ ህዳሴ ግድብ በተደረገ የገቢ ማሰባሰቢያ መርኃግብር ከ15 ሺህ ዩሮ በላይ ተሰበሰበ፡፡
ባሕር ዳር፡ ሐምሌ 19/2013 ዓ.ም (አሚኮ) በጀርመን ሙኒክ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን አስተባባሪነት “ደግሞ ለዓባይ” በሚል መሪ መልዕክት ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በተዘጋጀ የገቢ ማሰባሰቢያ መርኃግብር ከ15 ሺህ ዩሮ በላይ ተሰብስቧል፡፡
ኢትዮጵያውያኑና ትውልደ ኢትዮጵያውያኑ ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ገቢውን ያሰባሰቡት በቦንድ ግዥ፣ በመጽሔት ሽያጭና በስጦታ ነው።
በጀርመን ፍራንክፈርት የኢፌዴሪ ቆንስላ ጄነራል ጽሕፈት ቤት ቆንስል ጄኔራል ፈቃዱ በየነ በጀርመን ሙኒክ አካባቢ የሚኖሩ የኢትዮጵያ ኮሙኒቲ አባላት በሁሉም ዘርፍ ሀገራቸውን ሲደግፉ የነበሩ መሆናቸውን አውስተዋል።

ኢትዮጵያውያኑና ትውልደ ኢትዮጵያውያኑ ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል፡፡
በጀርመን ሙኒክ አካባቢ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የቦንድ ግዢውን መፈጸማቸው ክብር እንደተሰማቸው ገልጸዋል፡፡ በቀጣይም በሁሉም ዘርፍ ድጋፋቸውን አጠናክረው በመቀጠል ለሀገራቸው ያላቸውን ፍቅር በተግባር እንደሚያሳዩ መናገራቸውን ከኢትዮጵያ ዲያስፖራ ኤጀንሲ የተገኘ መረጃ ያመላክታል፡፡

ተጨማሪ መረጃዎችን ከአሚኮ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ