
በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ሪፈራል ሆስፒታል ያሉ ችግሮች እንዲቀረፉ እንደሚሠራ ጤና ሚኒስቴር ገለጸ፡፡
ባሕር ዳር፡ መጋቢት 25/2013 ዓ.ም (አሚኮ) “እኔም ያገባኛል” የሚል አንድምታዊ ትርጉም ያለውና ‹‹I care›› በሚል መጠሪያ በፌደራል ጤና ሚኒስቴር አማካኝነት የተቀረፀ ፕሮግራም በኢትዮጵያ የሚገኙ ሆስፒታሎችን ችግር የተለያዩ ባለ ድርሻ አካላትን በማስተባበር ለመቅረፍ እየሠራ ይገኛል፡፡ በሪፈራል ሆስፒታሉ ውስጥ ያሉና ተገቢ አገልግሎት ለሕዝቡ ለማድረስ መሰናክል የሆኑ ችግሮችን በመለየት ለተለያዩ ባለድርሻ አካላት እንዲመለከቱ ተደርጓል፡፡
የሪፈራል ሆስፒታሉ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዶክተር አሸናፊ ታዘበው ለባለድርሻ አካላት የሚደረገው ጉብኝትና ውይይት ሆስፒታሉ አገልግሎት ለመስጠት በተቸገረባቸው ጉዳዮች ላይ መፍትሔ ለመፈለግ ያለመ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ በሆስፒታሉ ውስጥ ያሉ ችግሮች ተለይተው በየዘርፉ እንደተደራጁና በጉብኝቱ የተጋበዙ ተቋማትም ችግሮችን ለመቅረፍ የሚጠበቅባቸውን የቤትሥራ ይወስዳሉ ነው ያሉት፡፡
በፌዴራል ጤና ሚኒስትር የእናቶችና የህፃናት ጤና እንዲሁም የሥርዓተ ምግብ ዳይሬክተር ዶክተር መሰረት ዘላለም የጎንደር ዩኒቨርሲቲ አጠቃላይ ሪፈራል ሆስፒታሉ ከ 5 ሚሊዮን በላይ ለሆነ ሕዝብ አገልግለት የሚሰጥ ቢሆንም ለህሙማን የህክምና አገልግሎት ለመስጠት እንቅፋት የሆኑ በርካታ ችግሮች አሉበት ብለዋል፡፡ የጤና ሚኒስቴርም ችግሮችን ለመቅረፍ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ተባብሮ እንደሚሠራ ተናግረዋል፡፡
የህሙማን ስቃይ ሳይባባስ እና ተገቢውን አገልግሎት በመስጠት ለደንበኞችና ለህክምና ባለሙያዎች እርካታ እንዲያገኙ ሁሉም በያገባኛል ስሜት ተሳትፎ እንዲያደርግም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የፌደራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ብርሃኑ ፈይሳ በጎንደር ዩኒቨርሲቲ አጠቃላይ ሪፈራል ሆስፒታል ከሰው ሀብት አስተዳድር አኳያ ያሉ ችግሮችን በማየት ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር መፍትሔ እንደሚያፈላልጉ ገልጸዋል፡፡
የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት አስራት አፀደወይን (ዶ.ር) የ80 ዓመት እድሜ ያለው የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ስፔሻላይዝድ ሪፈራል ሆስፒታል ከ4 ሺህ በላይ ሀኪሞች፣ የጤና ባለሙያዎችና የአስተዳደር ሰራተኞች እንዳሉት ጠቁመዋል፡፡
ከፍተኛ የሕዝብ ቁጥር ባላት ጎንደር ከተማ ተጨማሪ ሆስፒታሎች ባለመኖራቸው ሪፈራል ሆስፒታሉ ከፍተኛ ጫና እንዲኖርበት ምክንያት መሆኑን አንስተዋል፡፡ በሆስፒታሉ ውስጥ የሚገኙ አብዛኞቹ ህንፃዎች ሆስፒታሉ ሲመሰረት የተገነቡ መሆናቸውና የተጀማመሩ አዳዲስ ህንፃዎች ተጠናቀው ወደ ሥራ አለመግባታቸውም በሆስፒታሉ ሥራ ላይ ጫና መፍጠሩን የጠቀሱት ዶክተር አስራት የ‹‹አይ ኬር›› መርኃግብር ዘርፈ ብዙ ችግሮችን ለመፍታት ተስፋ እንደተጣለበት ጠቅሰዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲውም ችግሮች እንዲፈቱ እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በሆስፒታሉ የተለዩ ችግሮች እንዲፈቱ ሁሉም ርብርብ እንዲያደርግ ጠይቀዋል፡፡
ዘጋቢ፡- ፍፁምያለምብርሃን ገብሩ – ከጎንደር
ተጨማሪ መረጃዎችን ከአብመድ የተለያዩ የመረጃ መረቦች ቀጣዮቹን ሊንኮች በመጫን ማግኘት ትችላላችሁ፡፡
በዌብሳይት www.amharaweb.com
በቴሌግራም https://bit.ly/2wdQpiZ