ባሕር ዳር: ግንቦት 05/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የአፍሪካ ከ17 ዓመት በታች እግር ኳስ ዋንጫ በየሁለት ዓመቱ የሚካሄድ እና ዕድሜያቸው 17 ዓመት እና ከዚያ በታች የኾኑ ተጫዋቾች የሚሳተፉበት ውድድር ነው፡፡
በእነዚህ ውድድሮች ካሜሩን፣ ጋምቢያ፣ ጋና፣ ማሊ እና ናይጀሪያ እያንዳንዳቸው ሁለት ሁለት ጊዜ ሻምፒዮን ኾነዋል፡፡
ግብፅ፣ ቡርኪናፋሶ፣ ኮትዲቯር፣ ሴኔጋል እና ሞሮኮ ደግሞ አንድ አንድ ጊዜ ዋንጫውን የማንሳት ዕድል አግኝተዋል፡፡
የዘንድሮው 16ኛው የአፍሪካ ሀገራት ከ17 ዓመት በታች እግር ኳስ ዋንጫ ውድድር ከዛሬ ጀምሮ በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል፡፡
በውድድሩ 16 ሀገራት በአራት ምድቦች ተደልድለው የሚፎካከሩ ሲኾን ቀይ ቀበሮዎቹ በሚል ቅፅል ስም የሚጠራው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በመጀመሪያው ምድብ ከአስተናጋጇ ሞሮኮ፣ ግብጽ እና ቱኒዚያ ጋር ተደልድሏል፡፡
በምድብ 2 ኮትዲቯር፣ ካሜሩን፣ ኡጋንዳ እና ዲሞክራቲክ ኮንጎ፤
በምድብ 3 ማሊ፣ አንጎላ፣ ታንዛኒያ እና ሞዛምቢክ
በምድብ 4 ሴኔጋል፣ደቡብ አፍሪካ፣ አልጀሪያ እና ጋና ይገኛሉ፡፡
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ከዚህ በፊት በዚህ ውድድር ሦሥት ጊዜ ተሳትፏል፡፡ከፍተኛ ውጤቱ በ1997ቱ መድረክ አራተኛ ደረጃን ይዞ ያጠናቀቀበት ሲኾን ከዚያ ውጭ በተሳተፈባቸው ሁለት ውድድሮች የምድብ ጨዋታዎች ተሳትፎ አድርጎ ተመልሷል፡፡
ከ22 ዓመታት በኋላ ወደ ዘንድሮው ውድድር ተሳትፎ የተመለሱት ቀይ ቀበሮዎቹ ፉክክራቸውን ዛሬ 10፡00 ላይ ከግብፅ ጋር በሚያደርጉት ጨዋታ ይጀምራሉ፡፡
በዚህ ውድድር ከ1ኛ እስከ 10ኛ ደረጃን ይዘው የሚያጠናቅቁ ሀገራት ኳታር ላይ በሚካሄደው የ2026 የፊፋ ከ17 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ አፍሪካን ወክለው የሚሳተፉ ይኮናል፡፡
በኃይሌ አበራ
የአሚኮ ዲጅታል ቤተሰብ ይሁኑ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን !



