
የባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት 20ኛ መደበኛ ጉባኤ እየተካሄደ ነው።
በጉባኤው መክፈቻ የ2012 በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ቀርቧል። በሥራ እድል ፈጠራ 30 ሺህ 365 ሰዎች የሥራ እድል እንዲፈጠርላቸው ለማድረግ ታቅዶ ለ37 ሺህ 537 ሰዎች የሥራ እድል መፈጠሩን የባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አማረ ዓለሙ ተናግረዋል።
በማኑፋክቸሪንግ፣ በኮንስትራክሽን፣ በግብርና፣ እንስሳትና ዓሳ ሀብት ልማትና በሌሎች ዘርፎች ነው የሥራ እድሎቹ የተፈጠሩት።
በመሠረተ ልማት ግንባታው 9 ነጥብ 1 ኪ.ሜ ጌጠኛ ድንጋይ ንጣፍ ለመሥራት ታቅዶ 8 ነጥብ 85 ኪ.ሜ መሠራቱን ምክትል ከንቲባው አስታውቀዋል።
ሕገ ወጥ ግንባታን በማስቆም ደንብ ማስከበርን በተመለከተም 38 ሺህ 248 የተለያዩ ሕገ ወጥ ግንባታዎችን ማስወገድ እንደተቻለ አቶ አማረ አንስተዋል። በቅጣት 1 ነጥብ 4 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ገንዘብ ለከተማ አስተዳደሩ ገቢ ማድረግ መቻሉንም ምክትል ከንቲባው ገልጸዋል።
ጉባኤው ዛሬ 21/01/2013 ዓ.ም ጀምሮ ለሦስት ቀናት ሲዘልቅ የ2013 በጀት ዓመት እቅድና የተለያዩ ሹመቶችን መርምሮ ያጸድቃል ተብሎ ይጠበቃል።
ዘጋቢ፦ ኪሩቤል ተሾመ