ከ129 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመቱ ሕገ ወጥ ዕቃዎችን በሕግ ቁጥጥር ስር ማዋሉን የገቢዎች ሚኒስቴር አስታወቀ።

308

በሕገ ወጥ መንገድ ሲዘዋወር የተያዘ ወርቅ
ባሕር ዳር፡ ነሐሴ 16/2012 ዓ.ም (አብመድ) ባለፉት 16 ቀናት ብቻ ግምታቸው ከ129 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጡ የኮንትሮባንድ ዕቃዎች፣ የታክስ ማጭበርበሮችና ህገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውሮችን በሕግ ቁጥጥር ስር መዋሉን ገቢዎች ሚኒስቴር አስታውቋል።

ለመንግሥት ገቢ ከተደረጉ ዕቃዎች ውስጥ በወቅቱ ምንዛሬ ተመን 17 ነጥብ 8 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያለው 449 ሺህ 700 የአሜሪካ ዶላር በሁመራ መስመር በቁጥጥር ስር ሲውል 46 ሚሊየን ብር ግምታዊ ዋጋ ያለው 23 ሺህ ግራም ወርቅ ደግሞ በቦሌ ኤርፖርት በኩል ከሀገር ሊወጣ ሲል በቁጥጥር ስር ውሏል፡፡

ሌሎች በቁጥጥር ስር ከዋሉት ዕቃዎች መካከል የተለያዩ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎች፣ አልባሳት፣ ሞተር ሳይክሎች፣ የጦር መሳሪያዎች፣ ጌጣጌጦች፣ አደንዛዥ ዕፆች፣ በቱሪስት ስም እና በህገ-ወጥ መንገድ የገቡ ተሽከርካሪዎች እና ሌሎች ዕቃዎች ይገኙበታል ብሏል ሚኒስቴሩ።

ሊጭበረበር የነበረን ታክስም በክትትል በመያዝ ገቢ መደረጉን ሚኒስቴሩ በማኅበራዊ የትሥሥር ገጹ አስታውቋል፡፡

ግምታዊ ዋጋ ውስጥ ያልተካተቱ ክላሽንኮቭ፤ የክላሽንኮቭ ካዝና፣ የክላሽ ጥይቶች፣ ሽጉጦች፣ የሽጉጥና የብሬን ጥይቶች በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በህገ-ወጥ መንገድ ሲዘዋወሩ በቁጥጥር ስር መዋላቸውም ተመላክቷል፡፡

ዕቃዎቹ በሀረር፣ ሞጆ፣ ባሕር ዳር፣ ሞያሌ፣ ድሬዳዋ፣ ቡሌ ሆራ፣ ኮምቦልቻ ፣ቦሌ ኤርፖርት፣ ጭናክሰን ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶች እና መቆጣጠሪያ ጣቢያዎች እንዲሁም በሌሎች አካባቢዎች የተለያዩ ስልቶችን በመጠቀም ወደ ሀገር ለማስገባትና ከሀገር ለማስወጣት ሙከራ ሲደረግ የተያዙ ናቸው፡፡

የኮንትሮባንድ ዕቃዎቹን በመያዙ ረገድ የጉምሩክ ኮሚሽን አመራሮችና የፍተሻ ባለሙያዎች፣ የፌደራል ፖሊስ፣ የሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ በክልል የሚገኙ የጸጥታ አካላትና የየአካባቢው ማኅበረሰብ ሚና የጎላ እንደነበረም ተገልጿል።

Previous articleበአማራ ክልል በ 14 ቀናት ለ 60 ሺህ 514 ናሙናዎች የላቦራቶሪ ምርመራ መከናወኑን ቢሮው ገለጸ።
Next articleበኩር ነሀሴ 18/2012