በመጪው መስከረም እምቦጭ አረምን ከጣና ሀይቅ ለማስወገድ የሚያስችል የዘመቻ ሥራ እንደሚከናወን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ገለጹ።

681

ባሕር ዳር፡ ነሐሴ 9/2012 ዓ.ም (አብመድ) የእምቦጭ አረምን በዘላቂነት ለመከላከልና ለመቆጣጠር ያስችላል ተብሎ በተዘጋጀው ስትራቴጂክ ዕቅድ ላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በተገኙበት ውይይት ተደርጓበታል።

ስትራቴጂክ ዕቅዱ አረሙን ማስወገድ፣ በዘላቂነት የውኃና አካባቢ ጥበቃ መሥራትና ነፃ የሀይቅ ዳርቻ መሥራት እንዲሁም በሀይቁ ዙሪያ የሚኖሩ አርሶ አደሮችን የኑሮ ሁኔታ ማሻሻል ላይ ትኩረት ያደረገ ነው።

በዕቅዱ ላይ ገለጻ ያደረጉት የውኃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ስለሺ በቀለ (ዶክተር ኢንጂነር) የእምቦጭ አረም በ1956 ዓ.ም በአባ ሣሙዔል ግድብ ለመጀመሪያ ጊዜ የታየ መጤ ወራሪ አረም መሆኑን አስታውሰዋል።

ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ በጣና ሀይቅ ላይ አረሙ በፍጥነት እየተስፋፋ መሆኑንና በሰባት ወረዳዎችና 35 ቀበሌዎች መዳረሱንም ተናግረዋል።

እምቦጭ አረም በብዝሃ ሕይወት አንዲሁም በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስኮች ላይ የደቀነው ሥጋት ከፍተኛ መሆኑንም ሚኒስትሩ ገልጸዋል።

በጣና ሀይቅና በአጠቃላይ በጣና ተፋፈስ ዙሪያ የእርሻ መስፋፋት፣ የውኃ አካላት ላይ የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች፣ ከከተማና ከኢንዱስትሪ ወደ ጣና ሀይቅ የሚገቡ ፍሳሾች አረሙ እንዲስፋፋ አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆኑንም ነው ያብራሩት።

ይሁንና አረሙን ማስወገድ የሚቻለው ልማዳዊ ከሆነ አሰራር ወጥቶ ስትራቴጂውን ተግባራዊ በማድረግ መሆኑን በመግለፅ ለዚህም በጋራ መሥራት እንደሚገባ አሳስበዋል።

የተለያዩ አገሮችን ተሞክሮች በማየት እምቦጭ አረምን ለኃይል አማራጭነት መጠቀም እንደሚቻል መግለፃቸውንም ኢዜአ ዘግቧል።

የእምቦጭ አረምን ለመከላከል በጣና ተፋፈስ ዙሪያ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት እየተከናወነ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ በተለይም የተለያዩ ፈሳሾችና ንጥረ ነገሮች ወደ ሀይቁ እንዳይገቡ የማድረግ ተግባር ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

Previous articleበናይል ተፋሰስ ሀገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በተፋሰሱ ሀገራት መካከል ታላቁ የሕዳሴ ግድብን በተመለከተ የጠራ የጋራ ግንዛቤና አቋም እንዲኖር ለማድረግ እንዲሠሩ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ጥሪ አቀረቡ።
Next articleየኢትዮጵያ ኤርፖርቶች ድርጅት ከ 97 ሚሊዮን ብር በላይ ውዝፍ እዳ ለጎንደር ከተማ አስተዳደር እንዲከፍል የፍርድ ቤት ውሳኔ ተላለፈ።