
ኢትዮጵያ በዓለም የጤና ድርጅት የተጀመረውን የአፍ እና የአፍንጫ መሸፈኛን የሚያስተዋውቅ ዘመቻ ተቀላቀለች።
ኢትዮጵያ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን የመከላከል ሥራውን አጠናክሮ ለማስቀጠል በዓለም የጤና ድርጅት የተጀመረውን የአፍ እና የአፍንጫ መሸፈኛን የሚያስተዋውቅ ዘመቻ ተቀላቀለች።
ዘመቻውም “ማስክ ኢትዮጵያ” ተብሎ ተሰይሟል::
ይህንንም የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ማስጀመራቸውን ጤና ሚኒስቴር ገልጿል። “በዚህ የአፍ እና የአፍንጫ መሸፈኛ ዘመቻ የሁላችንም ተሳትፎ ጨምሮ፣ እውቀታችን አድጎ፣ ባህሪያንም ተለውጦ፣ ወረርሽኙን በተሻለ አቅም መከላከል እንችላለን ብዬ አምናለሁ” ብለዋል ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ባስተላለፉት መልእክት፡፡
“ሁላችንም፣ የአፍ እና አፍንጫ መሸፈኛን በብዛት በማምረት፣ በትክክል በማድረግ ራሳችንንም፣ ወገኖቻችንንም ከበሽታ እንጠብቅ!” ሲሉ ጥሪ ማቅረባቸውንም ከጽሕፈት ቤታቸው ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።
አንድም ሰው በበሽታ እንዳይያዝ ፣ የማይተካ ሕይወት እንዳያልፍ እና የአገር እድገት እንዳይስተጓጎል ማድረግ እንደሚገባም ነው ፕሬዝዳንቷ ያሳሰቡት።