
ደብረብርሃን: መጋቢት 18/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የልጅነት ልምሻ (ፖሊዮ) መከላከያ ክትባት ዘመቻ በደብረ ብርሃን ከተማ መስጠት ተጀምሯል።
ክትባቱ በአማራ ክልል ከመጋቢት 18/2018 ዓ.ም ጀምሮ እስከ መጋቢት 21/2018 ዓ.ም ድረስ ለተከታታይ አራት ቀናት ይሰጣል።
የአማራ ክልል የኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ስሜነህ አያሌው እንዳሉት በክልሉ ዕድሜያቸው ከ5 ዓመት በታች የኾኑ ከ2 ነጥብ 2 ሚሊዮን በላይ ሕጻናትን ለመከተብ ታቅዷል።
ክትባቱን የሚሰጡ ባለሙያዎች መሠማራታቸውንም ገልጸዋል። ክትባቱም ቤት ለቤት፣ በጤና ተቋማት፣ በክትባት ጣቢያዎች እና በትምህርት ቤቶች እንደሚሰጥ ተናግረዋል።
ፖሊዮ በሕጻናት ላይ የእግር እና የእጅ ጡንቻ መዛል፣ ሽባነት የሚያስከትል እና እስከ ሞት የሚያደርስ ጉዳት እንደሚያስከትል ገልጸዋል።
በሽታው በክልሉ ሁለት ከተሞች መከሰቱ በመረጋገጡ ወላጆች ለክትባቱ ትኩረት ሰጥተው ልጆቻቸውን ማስከተብ እንዳለባቸው አሳስበዋል።
ዘጋቢ፦ ብርቱካን ማሞ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
