
ባሕር ዳር: መጋቢት 17/2018 ዓ.ም (አሚኮ) በኢትዮጵያ ሕዝብ ዘንድ የአብሮነት እሴትን ከሚያጎለብቱ ባሕላዊ በዓላት አንዱ በሀረሪ ክልል በየዓመቱ በድምቀት የሚከበረው የሹዋሊድ በዓል አንደኛው ነው።
የዘንድሮው የሹዋሊድ በዓል በክልሉ ኅብረ-ብሔራዊ አንድነትን በሚያሳይ መልኩ እና የክልሉን ልማት እና እድገት የበለጠ ማጠናከር በሚያስችል መልኩ በደማቅ ዝግጅት እንደሚከበር የሀረሪ ክልል የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት አስታውቋል።
ይህ ባሕላዊ በዓል በክልሉ የመቻቻል፣ የአብሮነት፣ የሰላም እሴትን እና የቱሪዝም ዘርፉን ለማሳደግ ጠቀሜታው የጎላ ነው።
የዘንድሮውን የሸዋሊድ በዓል በተሳካ መልኩ ለማክበር የተለያዩ ኮሚቴዎች ተዋቅረው ሥራዎች ሲተገበሩ መቆየታቸው ተገልጿል። አሁን ላይ በዓሉን ባማረ እና በደመቀ መልኩ ለማክበር አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ተግባራት ሁሉ መጠናቀቃቸው ተገልጿል።
በበዓሉ ላይም የሀረሪን ታሪክ፣ እሴት እና ባሕልን ሊያስተዋውቁ እና ሊገልጹ የሚችሉ ዝግጅቶች በወንድማማችነት መንፈስ ለታዳሚው ይቀርባሉ ነው የተባለው።
የሀረሪ ክልል መንግሥት ለሹዋሊድ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፏል። በዓሉ አብሮነት፣ ፍቅር፣ ሰላም እና ወንድማማችነት የሚጠናከርበት እንዲኾንም ተመኝቷል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
