
ደሴ፡ የካቲት 19/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የደቡብ ወሎ ዞን
ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የማኒፈስቶ እና የምርጫ ምልክት የማስተዋወቂያ መርሐ ግብር በደሴ ከተማ አካሂዷል።
በመድረኩ ላይ መልእክት ያስተላለፋት የደቡብ ወሎ ዞን
ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኀላፊ ተስፋ ዳኛው ኢትዮጵያን ወደ ብልጽግና ጎዳና ለማምጣት ፍኖተ ካርታ ተቀርጾ እየተተገበረ መኾኑን አመላክተዋል።
የተሻለች ኢትዮጵያን ለመገንባት የሚያስችሉ በርካታ ሥራዎች እንደ ሀገር እየተከናወኑ መኾናቸውንም አብራርተዋል።
ብልጽግና ፓርቲ ተጨባጭ ሁለንተናዊ ለውጥን ያመጣና በቀጣይም የምንመኛት ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የሚያስችል አቅም ያለው ፓርቲ ነው ብለዋል።
ምርጫው ሰላማዊ እና ዴሞክራሲያዊ ኾኖ እንዲጠናቀቅ መሪዎች እና አባላት በትጋት እንዲሠሩም አሳስበዋል።
የደቡብ ወሎ ዞን ዋና አሥተዳዳሪ አሊ መኮንን ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ሕዝባዊ እና ሕጋዊ መንግሥት የምናጸናበት ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያን የበላይነት የምናረጋግጥበት ነው ብለዋል።
ብልጽግና ፓርቲ ፈተናዎችን ወደ ድል በመቀየር የሚያጓጉ አያሌ የልማት ለውጦችን ያስመዘገበ ፓርቲ ነው ያሉት ዋና አሥተዳዳሪው በምርጫው ዴሞክራሲያዊ ተወዳዳሪነቱን አጠናክሮ እንደሚያስቀጥልም አንስተዋል።
ምርጫው ነጻ፣ ሰላማዊ፣ ፍትሐዊ እና ተአማኒነት ያለው ኾኖ እንዲጠናቀቅ መላው ማኅበረሰብ የበኩሉን አስተዋጽኦ እንዲያበረክትም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
በመርሐ ግብሩ የብልጽግና ፓርቲ የምርጫ ምልክት የኾነውን የስንዴ ነዶ የማስተዋወቅ ፕሮግራም ተካሂዷል።
ዘጋቢ፦ ሙሐመድ በቀለ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
