
ገንዳ ውኃ፡ የካቲት 19/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የምዕራብ ጎንደር ዞን ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የሰባተኛውን ጠቅላላ ምርጫ ማኒፌስቶ እና የምርጫ ምልክት በገንዳ ውኃ ከተማ አስተዋውቋል።
የምዕራብ ጎንደር ዞን የብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኀላፊ እንዳለው ማሩ ሁለተናዊ ብልጽግና በኢትዮጵያ እንዲረጋገጥ ጉዞ መጀመሩን ገልጸዋል።
ፓርቲው በርካታ ለውጦች እና ስኬቶች እንደሚመዘገቡ ማድረጉን ተናግረዋል። በቀጣይም በርካታ ሥራዎችን እንደሚሠራ አመላክተዋል።
የብልጽግና ፓርቲ የምርጫ ምልክት የስንዴ ነዶ መኾኑን ያነሱት ኀላፊው የስንዴ ነዶ ምልክትም የአንድነት እና የብልጽግና ተምሳሌት እንደኾነ ገልጸዋል።
ሁሉም መሪ እና አባላት ምርጫው ሰላማዊ እና ፍትሐዊ በኾነ መንገድ እንዲፈጸም የበኩላቸውን ድርሻ መወጣት እንደሚጠበቅባቸውም አስገንዝበዋል።
የምዕራብ ጎንደር ዞን ዋና አሥተዳዳሪ እያሱ ይላቅ የሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መሠረት የሚጣልበት፣ ተምሳሌታዊት ሀገር የሚገነባበት፣ የሕዝብ ሉዓላዊነት በተግባር የሚረጋገጥበት እንዲኾን ልዩ ትኩረት በመስጠት እየተሠራ መኾኑን ገልጸዋል።
ምርጫ ዜጎች ይመራኛል፣ ያሥተዳድረኛል እና ሀገሪቱን ወደ ተሻለ የዕድገት ደረጃ ከፍ ያድርጋታል ብለው የሚያምኑበትን መሪ በዴሞክራሲያዊ መንገድ በድምጽ አሰጣጥ የሚመርጡበት ሥርዓት ነው።
ምርጫው ዴሞክራሲያዊ፣ ሰላማዊ፣ ፍትሐዊ እና በማኅብረሰቡ ዘንድ ተአማኒ በኾነ መልኩ እንዲከናወን ሥራዎች እየተሠሩ መኾኑንም አስረድተዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
