በሕገ ወጥ የሰው አዘዋዋሪዎች ምክንያት የስንቱ ሕይወት ተመሰቃቅሎ ይኾን?

9
ባሕር ዳር: የካቲት 10/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ሰውን በሕገ ወጥ መንገድ ድንበር ማሻገር፤ ለግል ጥቅም በማሰብ ሰውን በሕገ ወጥ መንገድ ወደ ሀገር እንዲገባ፤ ከሀገር እንዲወጣ፣ ከአንድ ሀገር ወደ ሌላ ሀገር ግዛት የማስተላለፍ ድርጊትን የሚያጠቃልል ዓለም አቀፋዊ ወንጀል ነው፡፡
ወንጀሉ በዛቻ፣ በኃይል፣ በማገት፣ በመጥለፍ፣ በማታለል ወይም ሥልጣንን ያለ አግባብ በመጠቀም ሊፈጸም ይችላል። በዚህ ሂደት በርካታ ዜጎችን ለኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ ቀውስ የሚዳርግ፤ ለሰብዓዊ መብት ጥሰት እና ለሞት የሚዳርግ ጉዳይም ነው።
የዚህ ወንጀል ሰለባ የኾኑት ባለታሪካችን አቶ አዛናው አያናው በምዕራብ ጎንደር ዞን ገንዳ ውኃ ከተማ ነዋሪ ናቸው። በ2016 ዓ.ም ልጃቸው በሕገ ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች ታፍኖ እንደተወሰደባቸው ለአሚኮ ተናግረዋል።
ልጃቸውን አፍነው ከወሰዱት በኋላ አዘዋዋሪዎች “ወደ ሊቢያ ልናሻግረው ነው፤ ገንዘብ አስገባልን፤ የማታስገባ ከኾነ እንገለዋለን” በሚል ማስፈራሪያ እና ዛቻ እንዳደረሱባቸው ይገልጻሉ።
አቶ አዛናው እንደሚናገሩት የልጃቸውን ሕይወት ለመታደግ የሚችሉትን ሁሉ አድርገዋል። ለዚህም ያላቸውን ሀብት ንብረት ሽጠዋል። ከዘመድ እና ከአካባቢው ማኅበረሰብ ሳይቀር ለምነው የልጃቸውን ሕይወት ለመታደግ ጥረዋል። ብዙ መስዋዕትነትንም ከፍለዋል። በየዙሩ ለሚቀባበሉት ሕገ ወጥ ደላሎች ከ4 ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር በላይ መክፈላቸውን በቁጭት እና በሀዘን ስሜት ነግረውናል።
ልጃቸውን ከሞት ቢታደጉትም ለቤቱ ማብቃት ግን አልተቻለም። ልጃቸው በከፍተኛ እንግልት ከቤቱ ከወጣ ከ2 ወራት ስቃይ በኋላ ወደ ሊቢያ ልከውታል። የከፋ የሥነ ልቦና ጫናም እንደደረሰበት ነው የነገሩን።
አቶ አዛናው እንደገለጹት የወንድማቸው ልጅም በተመሳሳይ ሀገር ሰላም ብሎ ሥራውን ከሚሠራበት ቦታ ታፍኖ ከፍተኛ ገንዘብ ተጠይቆበት በሕገ ወጥ አዘዋዋሪዎች ወደ ሊቢያ ሄዶ ቀርቷል።
✍️ ልክ እንደ አቶ አዛናው ሁሉ ስንቶች ልጆቻቸው በሕገ ወጥ አዘዋዋሪዎች ሰለባ ኾነው ይኾን?
✍️ ሰውን በሕገ ወጥ መንገድ ድንበር ስለማሻገር ወንጀል ሕጉስ ምን ይላል?
በኢትዮጵያ ወንጀሉን ለመከላከል እና ወንጀል ፈጻሚዎችን በሕግ ተጠያቂ ለማድረግ አዋጅ ቁጥር 1178/12 ወጥቶ በሥራ ላይ ይገኛል፡፡ በዚህ አዋጅ እንደተደነገገው:-
👉 ማንኛውም ሰው ሰውን በሕገ ወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ እንዲገባ፣ ከኢትዮጲያ እንዲወጣ፣ በኢትዮጵያ ግዛት እንዲተላለፍ ወይም ከኢትዮጵያ ለማስወጣት ዝግጅት ያደረገ፣ በሂደት ላይ የተገኘ፣ ያጓጓዘ ወይም የተቀበለ ከ5 ዓመት እስከ 10 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት እና ከ10 ሺህ እስከ 100 ሺህ ብር በሚደርስ የገንዘብ መቀጮ እንደሚያስቀጣ ሕጉ ይደነግጋል፡፡
👉 የወንጀል ድርጊቱ የተፈጸመው በሕጻናት፣ በአዕምሮ ሕሙማን፣ በአካል ጉዳተኞች ላይ ከኾነ፤ አደንዛዥ ዕፅ፣ መድኃኒት ወይም የጦር መሣሪያ በመጠቀም ከኾነ፤ በመንግሥት ባለሥልጣን ወይም ሠራተኛ ከኾነ እና ወንጀሉን የፈጸመው የተሰጠውን ኀላፊነት መከታ በማድረግ ከኾነ፤ ፈቃድ ያለው ሰው ፈቃዱን ሽፋን በማድረግ ከኾነ ከ7 ዓመት እስከ 15 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት እና ከ20 ሺህ እስከ 150 ሺህ ብር በሚደርስ የገንዘብ መቀጮ ያስቀጣል ይላል ሕጉ፡፡
👉 በተጎጂው ላይ ከባድ የአካል ጉዳት፣ የማይድን በሽታ ወይም ዘላቂ የአዕምሮ ጉዳት ያስከተለ፤ በተደራጀ የወንጀል ቡድን አባል የተፈጸመ ከኾነ ከ10 ዓመት እስከ 20 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት እና ከ30 ሺህ እስከ 150 ሺህ ብር በሚደርስ የገንዘብ መቀጮ ያስቀጣል።
👉 በተጎጂው ላይ ሞትን ያስከተለ እንደኾነ እንደ ሁኔታው ከ15 ዓመት እስከ 25 ዓመት፣ የዕድሜ ልክ ጽኑ እስራት፣ ሞት እንዲሁም ከ50 ሺህ እስከ 200 ሺህ ብር እንደሚያስቀጣም ተቀምጧል፡፡
ዘጋቢ:- አሰፋ ልጥገበው
አሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
Previous articleየብልጽግና ፓርቲ የማኒፌስቶ እና የምርጫ ምልክት በአማራ ክልል ደረጃ ይፋ የማድረጊያ መድረክ እየተካሄደ ነው።
Next article‎የኮኮብ መስክ-መርሐቤቴ የአስፋልት መንገድ ግንባታ የት ደረሰ?