
ደብረ ብርሃን: የካቲት 01/2018 ዓ.ም (አሚኮ) በምንጃር ሸንኮራ ወረዳ አረርቲ ከተማ የ”ኢትዮጵያ ታምርት፣ እኛም እንሸምት” መድረክ እየተካሄደ ነው፡፡
የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኀላፊ እንድሪስ አብዱ አምራች ኢንዱስትሪውን ለማነቃቃት በተሠራው ሥራ አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል።
ዘርፉን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ዋና ዋና የማነቆ ችግሮችን የመፍታት ሥራ በትኩረት እየተሠራ መኾኑን አመላክተዋል። አዳዲስ ኢንቨስትመንቶች ወደ ክልሉ እንዲመጡ እና በስፋት እንዲያመርቱ ምቹ ሁኔታዎች እየተመቻቹ መኾኑንም ገልጸዋል።
የክልሉን የኢኮኖሚ መዋቅር ታሳቢ ያደረጉ የሪፎርም ሥራዎች መከናወናቸውንም አቶ እንድሪስ አክለው ገልጸዋል። በዚሁ መሰረት “ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ ከመጀመሩ በፊት የነበረው 46 ነጥብ 2 በመቶ የማምረት አቅም አሁን ላይ ወደ 62 ነጥብ 4 በመቶ ከፍ ብለዋል።
ይህ የ16 ነጥብ 2 በመቶ ዕድገት በክልሉ የኢንዱስትሪ ልማት ላይ ትልቅ መነቃቃት መፈጠሩን ማሳያ መኾኑ ተጠቁሟል።
ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ 35 አምራች ኢንዱስትሪዎች ወደ ሥራ በመግባት ውጤታማ ተግባራትን ማከናወናቸውን አሳውቀዋል። ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርቶች ለመተካት የተያዘው ግብ ስኬታማ እየኾነ መምጣቱንም አስረድተዋል።
ክልሉ ያለውን የኢንቨስትመንት ጸጋ በመጠቀም ለሀገር ኢኮኖሚ ዕድገት ያለውን ድርሻ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።
ዘጋቢ:- ስንታየሁ ኀይሉ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
