
ደብረ ብርሃን፡ ጥር 28/2018 ዓ.ም (አሚኮ)የሰሜን ሸዋ ዞን ፍትሕ መምሪያ የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም ግምገማ እና የቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ እያካሄደ ነው።
የሰሜን ሸዋ ዞን ፍትሕ መምሪያ ኀላፊ ደመረ ቸሬ በበጀት ዓመቱ አጋማሽ የፍትሕ አገልግሎትን ለማጠናከር ሰፊ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በተለይም የማኅበራዊ ፍርድ ቤት ዳኞችን አቅም መገንባት እና የተጠያቂነት አሠራርን ማስፈን ላይ ስኬታማ ሥራዎች መሠራታቸውን ጠቁመዋል።
ከዚህም በተጨማሪ በወንጀል የተመዘበረ የመንግሥት እና የሕዝብ ሃብትን ማስመለስ፣ የንቃተ ሕግ ትምህርቶችን መስጠት እና ነጻ የሕግ ድጋፍ አገልግሎቶች በስፋት መከናወናቸውን ገልጸዋል።
የአማራ ክልል ፍትሕ ቢሮ የደብረ ብርሃን ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ኀላፊ ገዛኸኝ አበበ የ25 ዓመቱ የልማት እና የአሻጋሪ ዕቅድ ግቡን እንዲመታ ቅንጅታዊ አሠራር ወሳኝ መኾኑን ተናግረዋል።
በፍትሕ ተቋማት የሚታየው የአገልግሎት አሰጣጥ ከጊዜ ወደ ጊዜ መሻሻሉን የጠቀሱት ኀላፊው በቀጣይም ከዕቅድ ዝግጅት ጀምሮ እስከ ክትትል እና ድጋፍ ድረስ ያሉ አሠራሮችን በማጠናከር የሕዝቡን እርካታ ማረጋገጥ እንደሚገባ አመላክተዋል።
በግምገማ መድረኩ ላይ ባለፉት ስድስት ወራት በተከናወኑ ሥራዎች የተሻለ አፈጻጸም ያስመዘገቡ የደብረ ብርሃን ከተማ አሥተዳደር፣ አንጎለላና ጠራ፣ መራሃቤቴ እና መንዝ ጌራ ወረዳዎች በምሳሌነት ተጠቅሰዋል።
እስከ ጥር 29/2018 ዓ.ም ድረስ በሚቆየው በዚህ መድረክ ላይ ከዞን እና ከወረዳዎች የተውጣጡ ከፍተኛ መሪዎች እና የፍትሕ አካላት በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
ዘጋቢ፦ ፋንታነሽ መሐመድ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
