
ባሕር ዳር: ጥር 23/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ሪዞርቱ የገበታ ለትውልድ ዋነኛ ፕሮጀክት ነው። በ385 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ ነው፡፡ በአንድ ጊዜ እስከ 400 እንግዶችን ማስተናገድ የሚችሉ ሦስት ምግብ ቤቶች፣ ልዩ የባሕል ማዕከል፣ ዘመናዊ የክብረ በዓላትና የስብሰባ አዳራሾች፣ የሕፃናት መጫወቻ ሥፍራዎችና 15 ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር የሚረዝሙ የእግረኛ መንገዶችን የያዘው የሸበሌ ሪዞርት፤ ማኅበራዊ ትስስርን ለማጠናከር ታሳቢ ተደርጎ የተገነባ ነው።
10 ሺህ የፍራፍሬ ተክሎች ካረፉበት የፍራፍሬ ፓርክ ጀምሮ እስከ ዋናው የግመል ፓርክ ድረስ፤ እያንዳንዱ የሪዞርቱ ገጽታ የኢትዮጵያን ተፈጥሯዊና ባሕላዊ ሃብት የሚያንፀባርቅ ነው ተብሏል።
በ51 የተጠናቀቁ የመኝታ ክፍሎችና በዓለም አቀፍ ደረጃ በሚገኙ የቱሪዝም አገልግሎቶች እውን የኾነው ሸበሌ ሪዞርት፤ ኢትዮጵያን በአፍሪካ ቀዳሚ የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ በሚደረገው ጉዞ ውስጥ ትልቅ ታሪካዊ እጥፋት ነው።
ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የተገኘው መረጃ እንደሚያመላክተው ይህ ፕሮጀክት ሕልምን ወደ እውነት የመለወጥ፤ የኢትዮጵያን የተፈጥሮና የባሕል ጸጋዎች መላው ዓለም የሚካፈለው ቅርስ የማድረግ የመደመር መንፈስ በተግባር የታየበት ታላቅ ሥራ ነው፡፡
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
