
አዲስ አበባ: ጥር 21/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ከፌዴራል እና አዲስ አበባ ኅብረት ሥራ ኮሚሽኖች 360 የኅብረት ሥራ ማኅበራት የሚሳተፉበት ባዛር እና ኤግዚቢሽን ከጥር 25/2018 ዓ.ም እስከ ጥር 30/2018 ዓ.ም ለተከታታይ አምስት ቀናት በዓድዋ ሙዚየም ይካሄዳል።
የኤግዚቢሽኑ እና ባዛሩ ዋና ዓላማ አምራች እና ሸማቹን ማኅበረሰብ ማገናኘት፤ ምርትን በጥራት እና በተመጣጣኝ ዋጋ ማቅረብ፣ በቂ ምርት መኖሩን ለማሳዬት እና የገበያ ትስስር ለመፍጠር መኾኑን የኢትዮጵያ ኅብረት ሥራ ኮሚሽን እና የአዲስ አበባ ኅብረት ሥራ ኮሚሽን በጋራ በሰጡት የጋራ መግለጫ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ኅብረት ሥራ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሽሰማ ገብረ ስላሴ በዕለቱ በአጠቃላይ 360 የኅብረት ሥራ ማኅበራት ምርት እና አገልግሎታቸውን ይዘው ይቀርባሉ ብለዋል።
የአዲስ አበባ ኅብረት ሥራ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ተጫነ አዱኛ በባዛር እና ኤግዚቢሽኑ ከሚሳተፉ 360 የኅብረት ሥራ ማኅበራት ውስጥ 164ቱ ከአዲስ አበባ ኅብረት ሥራ ኮሚሽን እንደኾኑ ገልጸዋል።
በዕለቱም ከ25 ሚሊዮን ብር በላይ ግብይት ይካሄዳል ነው ያሉት። የኅብረት ሥራ ማኅበራቱ የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት በተለይም በእሑድ እና ቅዳሜ ገበያዎች ምርቶችን በብዛት እና በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ሚናቸውን እየተወጡ እንደኾነም ተገልጿል።
ዘጋቢ፦በለጠ ታረቀኝ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
