
ባሕር ዳር: ጥር 07/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በማኀበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ኢትዮጵያ ከለውጡ ጋር በመጣ የቱሪዝም ንጋት እየደመቀች እና እየለማች ነው ብለዋል።
የኢትየጵያ የዘመናት የቱሪዝም መዝገብ ሲገለጥ የሚነበበው በልኩ ያልደመቀ መልክዓ ተፈጥሮ፣ በወጉ ያልተገለጠ የታሪክ ግርማ፣ ሌማት ኸኖ ያልቀረበ ሃብት እና ውበት ነው።
ባለፉት የለውጥ ዓመታት በቱሪዝም ዘርፍ የመጣው ለውጥ ይህንን ሁሉ የዘመናት ችግር ከመሰረቱ የናደ አዲስ የቱሪዝም ልማት አምዶችን ያቆመ መኾኑን ገልጸዋል።
የለውጡ መንግሥት ቱሪዝምን እንደ አንድ የኢኮኖሚ መሠረት በመውሰድ በትጋት ሠርቷል፡፡ አሁን የድካሙ ፍሬ እየተሰበሰበ፣ የሃገራዊ ጥረቱ አዝመራ እየታጨደ ነው፡፡
ለዚህም ድንቅ ውጤት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ.ር) ዘርፉን በጠራ ራዕይ ተመልክተው፣ ለቱሪዝም የነበረውን እሳቤ ከማስተካከል ጀምሮ ሀገር እና ትውልድን ማዕከል ያደረገ አመራር በመስጠት የሠሩት ሥራ የስኬቱ በር ከፋች ነው ብለዋል።
ዛሬ በቱሪዝም ዘርፍ እያየን ያለነው ስኬት ሁሉ እንደ ቀን ንጋት የሚቆጠር የስኬት አሃዱ ነው፡፡
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
