
ባሕር ዳር: ታኅሣሥ 25/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የሚኤሶ – ድሬዳዋ የፍጥነት መንገድ ፕሮጀክት የሥራ ሂደትን በተመለከተ ከሚመለከታቸው የሥራ ኃላፊዎች ጋር ተወያይተዋል።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት የመንገድ መሠረተ ልማት የኢኮኖሚ ዕድገት ጉዟችን ቁልፍ ጉዳይ ነው ብለዋል።
ዛሬ የሚኤሶ – ድሬዳዋ የፍጥነት መንገድ ፕሮጀክት የሚገኝበትን የሥራ ሂደት በተመለከተ ከሚመለከታቸው የሥራ ኃላፊዎች ጋር ውይይት አካሂደናል ነው ያሉት።
በፕሮጀክቱ የሥራ ሂደት እየተከናወኑ የሚገኙ የሰው ኃይል ዝግጅት፣ የማሽነሪና ሌሎች የግንባታ ዕቃዎች አቅርቦት፣ የመስክ ዝግጅት እና ከአካባቢው ማኅበረሰብ ጋር የተደረጉ ውይይቶች ምን ይመስላሉ የሚሉትን አይተናል ብለዋል።
የሚኤሶ – ድሬዳዋ የፍጥነት መንገድ ፕሮጀክት ለከባድ የጭነት መኪኖች አዳጋች የነበረውን መንገድ ምቹ በማድረግ፣ የወጪና ገቢ ንግዳችንን ያቀላጥፋል፤ በቀጣናዊ ትስስር ረገድ ያለንን ሚናም ያጎለብታል ነው ያሉት።
ፕሮጀክቱ የኢኮኖሚያችንን ተወዳዳሪነትና የዜጎችን ኑሮ ለማሻሻል ጉልህ አበርክቶ የሚኖረው በመኾኑ በተያዘለት እቅድ መሠረት እንዲጠናቀቅ የተቀናጀ ርብርብ ማድረግ ይገባል ብለዋል በመልዕክታቸው።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
