
ባሕር ዳር፡ ታኅሣሥ 21/2018ዓ.ም (አሚኮ) በኢትዮጵያ በድምቀት ከሚከበሩ ሃይማኖታዊ በዓላት ውስጥ የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል አንዱ ነው።
በዓሉን በድምቀት ለማክበር የሚያስችለውን ቅድመ ዝግጅት ማድረጉን የላሊበላ ከተማ አሥተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ መሳይ ወዳጀ ገልጸዋል።
ከወጣቶች እና ከሀገር ሽማግሌዎች ጋር በመቀናጀት እንግዶች ወደ ተዘጋጀላቸው የማረፊያ ቦታ እንዲያርፉ እየተደረገ እንደሚገኝም ገልጸዋል።
እንግዶች በሚያርፉበት ቦታ ንጽሕናው የተጠበቀ የውኃ እና የምግብ እንዲሁም የመብራት እና የጤና አገልግሎት እንዲያገኙ ዝግጅት መደረጉንም አንስተዋል።
በዚህ ዓመት በተፈጠረው አንጻራዊ ሰላም ከባለፉት ዓመታ የተሻለ የጎብኝዎች እንቅስቃሴ መኖሩን ያነሱት ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው ለልደት በዓልም ከታኅሣሥ 18/2018 ዓ.ም ጀምሮ እንግዶች መግባት መጀመራቸውን ነው የገለጹት።
በበዓሉ ከባለፉት ዓመታት የበለጠ ቁጥር ያለው ታዳሚ እንደሚገኝም ነው የተናገሩት።
“የኢየሱስ ክርስቶስን የልደት በዓል ማክበር የምትፈልጉ ሁሉ ኑ! በጋራ እናክብር፤ እንቀበላቹሃለን” ብለዋል ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
