
ባሕር ዳር: ታኅሣሥ 15/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራው በ12 ቀበሌዎች በ24 ተፋሠሶች ይሠራል። ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው በማሥጀመሪያ መርኃ ግብሩ ላይ እንዳሉት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራ የሚከናወንባቸው ቀበሌዎች የዓባይ እና ጣና ተፋሰስ መሆናቸው ሐይቁ እና ወንዙ በደለል እንዳይሞሉ ወሳኝነት አለው ብለዋል።
የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኀላፊ መሰሉ ብርሃኑ በክልሉ በተለያዩ አካባቢዎች የተፋሰስ ሥራ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል። እስከአሁንም ከ1 ሺህ 600 በላይ በሆኑ ተፋሰሶች ከ3 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የተፋሠስ ሥራ ተሠርቷል ብለዋል። በዚህ ዓመትም ልማትን ሊያረጋግጥ በሚችል አግባብ ቀድመው የተሠሩትን ማጠናከር፤ በአዲስ የሚሠሩትን በጥራት መሥራት ትኩረት ይደረግበታል ብለዋል።
የዘንዘልማ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደሮች ባለፋት ዓመታት በተሠራው ሥራ መሬታቸው ለምነቱ ተመልሶ ምርታማነታቸው እንዲጨምር እንደረዳቸው አሥረድተዋል። የዚህን ዓመት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራም ዘላቂ ልማትን ሊያረጋግጥ በሚችል መንገድ እንደሚሠሩ ተናግረዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
