የታጣቂ ኀይሎች ለሰላም ቅድሚያ እንዲሰጡ ምሁራን ኅላፊነታቸውን እንዲወጡ ተጠየቀ። ‎

2

ጎንደር: ታኅሣሥ 14/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ‎”ለሀገረ መንግሥት ግንባታ የምሁራን ሚና” በሚል መልዕክት የጎንደር ዩኒቨርሲቲ መምህራን እና የአሥተዳደር ሠራተኞች ጋር ውይይት ተካሂዷል።

‎ዩኒቨርሲቲዎች ከመማር ማስተማር ባሻገር ፖሊሲ በመቅረጽ ለሀገር ግንባታ መሠረት መኾናቸውን ያስረዱት የጎንደር ዩንቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶክተር አስራት የኢትዮጵያን መጻኢ እድል ለመወሰን የምሁራን ሚና ወሳኝ ነው ብለዋል።

‎ምሁራን ሀገር ከገባችበት ችግር እንድትወጣ የበኩላችን ተወጥተናል ወይ? ብሎ ራስን መጠየቅ ይገባል ያሉት ዶክተር አስራት የሕዝብን ችግር መረዳት እና መፍትሄ ማበጀት እንደሚጠበቅ አስረድተዋል።

‎የጎንደር ዩኒቨርሲቲ በቀደሙት ዘመናት በሀገረ መንግሥት ግንባታ ሂደት ሚናውን የተወጣ ተቋም መኾኑን ያስረዱት የውይይቱ ተሳታፊዎች ሀገር ችግር ባጋጠማት ወቅትም አጋዥ እንደነበር ተናግረዋል።

‎ዩኒቨርሲቲው ከምርምር እና መማር ማስተማር ሥራው ባሻገር የማኅበረሰብ አቀፍ አገልግሎት እየሰጠ እንደኾነም ተሳታፊዎቹ ጠቁመዋል።

‎የዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ ለጎንደር ከተማ እድገት በሁሉም ዘርፍ እውቀታቸውን እና ሀሳባቸውን እያዋጡ ነውም ተብሏል።

‎የሀገር እድገት የሚወሰነው ሰላም ሲረጋገጥ በመኾኑ ታጣቂ ኀይሎች ለሰላም እጃቸውን እንዲዘረጉ መሥራት ከምሁራኑ የሚጠበቅ ጉዳይ መኾኑን ተሳታፊዎቹ አንስተዋል።

‎ለችግሮች መፍትሄ ለማበጀት ምሁራን አጋዥ ሊኾኑ እንደሚገባ ያመላከቱት የጎንደር ከተማ አሥተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ቻላቸው ዳኘው ለሀገረ መንግሥት ግንባታ መሪን የሚያበረታ ትችት ወሳኝ መኾኑን አመላክተዋል።

‎የምሁራን አቅም የከተማዋ እድገት ላይ አሻራ እያሳረፈ እንደሚገኝ የጠቀሱት አቶ ቻላቸው ስማርት ሲቲ እና ሌሎች ሥራዎች ማሣያ ስለመኾናቸው አንስተዋል።

‎የሰላም እጦቱ የክልሉን የመልማት እድል እያሳጣ መኾኑን የገለጹት ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው ለሰላም መስፈን የበኩላችሁን ልትወጡ ይገባል ሲሉ አሳስበዋል።

‎ያስተማረን ማኅበረሰብ ማገልገል ከሁሉም ይጠበቃል ያሉት አቶ ቻላቸው የጎንደር ዩኒቨርሲቲ በጎንደር ከተማ ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ እገዛ እያደረገ መኾኑንም አረጋግጠዋል።

ዘጋቢ:- ‎ደስታ ካሣ

‎የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Previous articleከ1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ እየሠራ መኾኑን የኦሮሞ ብሔረሰብ አሥተዳደር አስታወቀ።
Next articleበደብረ ማርቆስ የሰላም ጥሪን ተቀብለው ከመጡ ታጣቂዎች ጋር ውይይት ተካሂዷል።