“ሐጂ ማድረግ የሚያከስር ሳይኾን ሃብትንም የሚያበረክት ነው” ሼህ ኑረዲን ቃሲም

6
ባሕር ዳር: ታኅሣሥ 10/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት የ1447ኛውን ዓመተ ሂጅራ የሐጂ ምዝገባን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥቷል።
የከፍተኛ ምክር ቤቱ ዋና ጸሐፊ አሕመድ ካሣ ሙዘይን ለመላው ሙስሊም እንኳን ለ1447ኛው ዓመተ ሂጅራ የሐጂ ምዝገባ አደረሳችሁ ብለዋል።
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የ2018 ዓመተ ልደት የሐጂ ምዝገባ ከሕዳር 22 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በሁሉም የሀገራችን ክፍሎች የምዝገባ ጣቢያዎች መጀመሩን ገልጸዋል።
በአማራ ክልልም በባሕር ዳር፣ በደሴ እና በከሚሴ የሐጂ ምዝገባ ጣቢያዎች ተጀምሯል ነው ያሉት። ሐጂ ከእስልምና መሠረቶች ውስጥ አንዱ በመኾኑ ሐጂ የማድረግ ግዴታ ያለባቸው ሙስሊሞች መስፈርቱን በማሟላት በምዝገባ ጣቢያዎቹ ቀርበው እንዲመዘገቡ አሳስበዋል።
ለሐጂ የሚመዘገቡ ሙስሊሞች ጉርድ ፎቶ ግራፍ፣ ፓስፖርት፣ የቢጫ ወባ ክትባት፣ የልደት ካርድ እና ከጤና ተቋማት ሜዲካል ሰርተፍኬት መያዝ እንዳለባቸውም በመግለጫው ጠቅሰዋል። የዘንድሮ የሐጂ ጉዞ ክፍያ 740 ሺህ ብር እንደኾነም ተገልጿል።
ማንኛውም ሐጂን መፈጸም የፈለገ ሰው ከሚከተሉት አሥር በሽታዎች ነጻ መኾን አለበት።
👉 እጥበት የሚያስፈልገው የኩላሊት ድክመት
👉 የልብ ድካም
👉 ማንኛውም የሳንባ ህመም እና ኦክስጅን የሚያስፈልገው ከኾነ፣
👉 በማንኛውም ደረጃ የሚገኝ የጉበት ህመም
👉 ማንኛውም የአእምሮ ህመም፣
👉 በነርቭ ህመም የማገናዘብ ችሎታው የተጎዳ፣ እጅ እና እግሩን ማንቀሳቀስ የማይችል
👉 ከዕድሜ ጋር የተያያዘ የመርሳት እና የየዕለት ተግባርን ለመከወን የሚቸገሩ፣
👉 የካንሰር ህመም ኖሮበት ኬሞትራፒ የሚወስድ
👉 ለወሊድ ሦስት ወር የቀራት ነፍሰ ጡር
👉 በህክምና ላይ የሚገኝ እንደ ቲቪ እና መሰል ተላላፊ በሽታዎች ያሉበት መኾናቸውን በመግለጫው ተጠቅሰዋል። የአማራ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት በዘንድሮው ሐጂ ከ1 ሺህ በላይ ሁጃጆችን ለማስመዝገብ ታቅዶ እየተሠራ መኾኑንም ዋና ጸሐፊው በመግለጫቸው አሳውቀዋል።
ምዝገባውም እስከ ጥር 18/2018 ዓመተ ልደት ድረስ ብቻ በመኾኑ ሐጂ ለማድረግ ያሰቡ ሙስሊሞች እየቀረቡ እንዲመዘገቡ ጥሪ ተላልፏል።
የአማራ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሼህ ኑረዲን ቃሲም ባስተላለፉት መልዕክትም ሙስሊሞች ብዙ ተጉዘው እና ኖረው ሐጂን ይፈጽሙ እንደነበር አስታውሰዋል።
ገንዘቡ እና አቅሙ ላላቸው ሰዎች ሐጂ ግዴታ መኾኑንም አሏህ በቁርዓን ያስቀመጠው ነው ብለዋል። ሐጂን ብዙ ቱሩፋቶች ያሉት የእስልምና መሠረት ነው ያሉት ሼህ ኑረዲን ገንዘቡን በአግባቡ ተጠቅሞ ሐጂ ያደረገ ሰው እናቱ እንደወለደችው ሐጥያት እንደሌለበት ሰው ኾኖ እንደሚመለስ ሰለላህ አለሂ ወሰለም እንደተናገሩት ገልጸዋል።
ሐጂን የሚፈጽሙ ሰዎች የአሏህ ልዑካን ቡድኖች ኾነው እንደሚቆጠሩም ገልጸዋል። በሐጂ ሙስሊሞች በአንድነት በአረፋ ተራራ ላይ ለተመሳሳይ ተግባር፣ ተመሳሳይ ለብሰው፣ ተመሳሳይ እየተናገሩ በአንድ ቦታ ተሰባስበው የሚገኙበት ቦታ ነው ብለዋል።
“ሐጂ ማድረግ የሚያከስር ሳይኾን ሃብትንም የሚያበረክት” መኾኑን ተናግረዋል። እናም አቅሙ ያላቸው ሙስሊሞች ሐጂን እንዲተገብሩ አበረታትተዋል።
ዘጋቢ:- ዋሴ ባዬ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
Previous article“መመካከር እና መወያየት ለሰላም እሴት ግንባታ አስኳል ነው” ምክትል ርእሰ መሥተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ.ር)
Next articleንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት የጀመረበትን 10ኛ ዓመት እያከበረ ነው።