
ባሕር ዳር: ታኅሣሥ 08/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎች በምዕራብ ጎጃም ዞን ከቡሬ ከተማ እና ከቡሬ ዙሪያ ወረዳ ነዋሪዎች ጋር ተወያይተዋል።
የውይይቱ ተሳተፊዎች እኛ ግጭት እና ጦርነት አንፈልግም፤ ለዓመታት ተሰቃይተናል፤ ሰላም እንፈልጋለን፤ ጽንፈኝነትን እና ጽንፈኛውን አንፈልግም ነው ያሉት። በጫካ የወጣው ኃይል በእኛ ላይ መከራ አመጣ እንጂ ለሕዝብ የሚጠቅም ሃሳብ እና ተግባር የለውም ብለዋል።
ልጆቻችን ከትምህርት ገበታ ውጭ እንዲኾኑ፣ በነጻነት አልምተን እንዳንበላ አድርጎናል ብለዋል። ልጆቻችን ከትምህርት ብርሃን ርቀው በጨለማ እየኖሩ ነው፤ የልጆቻችን የነገ ተስፋ እያስጨነቀን ነው፣ በዚህ ከቀጠልን ነገ የአማራ ክልልን የሚመራ ሰው አይኖርም ነው ያሉት።
ጽንፈኛውን የሚደግፈውን ኃይል መታገል እና መዋጋት እንደሚገባ ተናግረዋል። የሀገር መከላከያ ሠራዊት የኢትዮጵያ ኩራት እና መከታ ነው፤ ሠራዊቱን መደገፍ ይገባል ነው ያሉት።
ችግሮች የሚፈቱት በውይይት እንጂ በጦርነት አይደለም ብለዋል። በመንግሥት ቢሮ ውስጥ ኾነው ጽንፈኛውን የሚደግፉ እና መረጃ የሚያቀብሉ ኃይሎችን ማጽዳት እንደሚገባ ተናግረዋል። ሕዝብን እያማረሩ እና ግጭት እንዲባባስ እያደረጉ ያሉ የመንግሥት የሥራ ኀላፊዎችን እና ባለሙያዎችን ማስተካከል እንደሚገባም አንስተዋል።
ጽንፈኛው ቡድን በሬዎቻችን ቀምቶ በልቷል፤ ንብረታችን ዘርፏል፤ ባለፉት ዓመታት ብዙ መከራ አይተናል ነው ያሉት። በየአካባቢያቸው ጥፋተኞችን እየታጋሉ እና ግፍን በቃን እያሉ መኾናቸውን ገልጸዋል።
መንግሥት በየዋሻው የተደበቀውን ጽንፈኛ እየተከታተለ እንዲያጸዳም ጠይቀዋል። በሚወስደው እርምጃ ተባባሪ እንደሚኾኑም ገልጸዋል። ራስን ከታጣቂ ቡድን ለማላቀቅ አንድነት እና በጋራ መነሳት እንደሚገባም ተናግረዋል።
መንግሥት የሰጠው የሰላም አማራጭ የሚደነቅ ነው፤ በጫካ የሚገኙ ኃይሎች የሰላም አማራጭን መቀበል አለባቸው ነው ያሉት። የሃይማኖት አባቶች እና የሀገር ሽማግሌዎች የታጠቁ ኃይሎች የሰላም አማራጭን እንዲቀበሉ ግፊት ማድረግ እንደሚገባቸው ተናግረዋል።
ጎጃም ባለው ጸጋ ልክ ተጠቃሚ እንዲኾን ሰላምን ማረጋገጥ ለነገ የሚባል ጉዳይ እንዳልኾነም ገልጸዋል። በገጠር የምንኖረው ሰዎች የምንበላው እስክናጣ ድረስ እየተሰቃየን ነው፤ ለልጆቻችን የምናጎርሰውን እየቀሙ እየበሉብን ነው፣ ወገኖቻችን እየታገቱ ገንዘብ አምጡ እየተባልን ነው ብለዋል።
ውይይቶችን እያሰፉ ዘላቂ ሰላምን ማረጋገጥ እንደሚገባም ተናግረዋል። ለእውነት እና ለሰላም በቁርጠኝነት እንነሳ፣ ለሰላም የሚከፈለውን ዋጋ እንክፈል ነው ያሉት።
ሕዝብን በማሰቃየት የሚፈታ ጥያቄ አለመኖሩንም ተናግረዋል። አማራ የሚያምርበት በአንድነት ሲኖር፣ በችግሩ ዙሪያ ሲመክር፣ የታላቅነቱን ልክ ሲያስጠብቅ ነው ብለዋል። የውስጥ ግጭት ለአማራ ሕዝብ ክብር፣ ታላቅነት እና ታሪክ እንደማይመጥንም አንስተዋል።
አባት እየተሰደበ፣ ሽማግሌ እየተዋረደ መኖር አይገባንም፤ መካሪ እና ዘካሪ እንድናጣ እየኾነ ነው ብለዋል። በግጭት የሚረጋገጥ ሰላም እና የሚሳካ ልማት አለመኖሩንም ተናግሯል።
ለኢትዮጵያ የሚጠቅመው ውስጣዊ እንደነትን ማጠናከር እና ሰላምን ማረጋገጥ መኾኑን ገልጸዋል። የውስጥ ግጭት ሀገርን ለውጭ ጠላት አሳልፎ የሚሰጥ ተግባር መኾኑን አመላክተዋል። ሰላምን በማረጋገጥ የልማት ሥራዎችን ማስቀጠል እንደሚገባም አመላክተዋል።
የቡሬ ከተማ አሥተዳደር ከንቲባ ደሳለው ፈቃድ ቡሬ የኢንዱስትሪ ከተማ ናት፤ ነገር ግን ዕድሉን እየተጠቀምን አይደለም፤ ይህ የኾነው ደግሞ ሰላማችን ባለመጠበቃችን ነው ብለዋል። ዘራፊውን እና ገዳይ ቡድኑን በግልጽ መቃወም እና መተጋል እንደሚገባ ተናግረዋል።
ያለውን ዕድል እና ጸጋ ለመጠቀም ሰላምን ማረጋገጥ እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል። የኢንዱስትሪ ከተማዋን ሰላም በመጠበቅ ከልማቱ ተጠቃሚ መኾን እንደሚገባም ተናግረዋል። በከተማዋ ውስጥ ሕዝብ የሚያነሳቸውን የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን ለመፍታት እየተሠራ መኾኑን ገልጸዋል።
የምዕራብ ጎጃም ዞን አሥተዳዳሪ እድሜዓለም አንተነህ የልማት እና የመልካም አሥተዳደር ጥያቄዎችን ለመፍታት ዘላቂ ሰላምን ማረጋገጥ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። የሕዝብ አሁናዊ እና ቀዳሚው ጥያቄ ሰላም መኾኑን ገልጸዋል።
ሰላምን ማረጋገጥ ቀዳሚው ጉዳይ ነው ያሉት አሥተዳዳሪው የሚዘርፈውን፣ ተማሪዎችን ከትምህርት ገበታ የሚያስቀረውን፣ መንገድ የሚዘጋውን፣ ሰው የሚገድለውን ጽንፈኛ ቡድን መታገል ይገባል ነው ያሉት።
እውነት ላይ በመቆም ግፍን ማውገዝ እና መጥፎ ድርጊትን መታገል እንደሚጠበቅም ገልጸዋል። ሰላምን ለማረጋገጥ ተከታታይ ውይይቶችን ማድረግ እና የጋራ መፍትሔ እያስቀመጡ መሄድ እንደሚገባ አመላክተዋል። ሕዝብን እያማረሩ የሚገኙ ባለሙያዎችን እና መሪዎችን እርምጃ በመውሰድ እንደሚያስተካክሉም አንስተዋል።
በየአካባቢው ያሉ ታጣቂዎች የሰላም አማራጭን እንዲቀበሉ ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል። ለጽንፈኛው ኃይል መረጃ በሚያቀብል እና ድጋፍ በሚያደርግ አካል ላይ እርምጃ እንደሚወስዱም አስገንዝበዋል። ሰላምን በማረጋገጥ የቡሬን ጸጋ መጠቀም እንደሚገባ ተናግረዋል።
ዘጋቢ:- ታርቆ ክንዴ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
