የጤና መድኅን አገልግሎት የመረዳዳት እና የጤና ዋስትና የሚረጋገጥበት ትልቅ ተግባር ነው።

9

ባሕር ዳር: ታኅሣሥ 05/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ‎የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ጤና መምሪያ የ2018 በጀት ዓመት የማኅበራዊ ጤና መድኅን አገልግሎት የንቅናቄ መድረክን እያካሄደ ነው።

‎‎የአማራ ክልል ጤና ቢሮ ኀላፊ አብዱልከሪም መንግሥቱ የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር በ2017 በጀት ዓመት በማኅበረሰብ አቀፍ ጤና መድኅን አገልግሎት ከፍተኛ አፈጻጸም ካላቸው ዞኖች አንዱ መኾኑን ተናግረዋል።

‎እንደ ክልል የጤና መድኅን ዘላቂ የጤና ፋይናንስ ሥርዓትን ለመገንባት አንዱ መውጫ በር ነው ብለዋል። ለዚህም የአካባቢን ሃብት ማሰባሰብ እና የተሰበሰበውን በአግባቡ መጠቀም ቁልፍ ጉዳይ መኾኑን ነው የተናገሩት።

‎የረጅ ድርጅቶች ድጋፍ እየቀነሰ መጥቷል ያሉት ኀላፊው የጤና ሥርዓቱን ዘላቂ እና የማይበገር ለማድረግ ዘላቂ የኾነ የውስጥ የፋይናንስ አቅም መገንባት ያስፈልጋል ነው ያሉት። ለዚህ ደግሞ የጤና መድኅን ዋና መሣሪያ ነው ብለዋል።

‎ጤና መድኅን ፍትሃዊ የኾነ የጤና አገልግሎትን ለሁሉም ለማዳረስ ቁልፍ ምክንያት ነው፤ “የመረዳዳት የጤና ዋስትና የሚረጋገጥበት ትልቅ ተግባር መኾኑንም” ነው የገለጹት።

‎በዚህ ዓመት ሁሉም የከተማ ነዋሪ አባል እንዲኾን የተያዘውን ግብ ለማሳካት የሚመለከታቸው አካላት ርብርብ ማድረግ እንዳለባቸው ገልጸዋል። የጤና መድኅን ተግባራትን በቁርጠኝነት በመሥራት በአንድ ወር ውስጥ እንዲጠናቀቅ ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

‎የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው በከተማ አሥተዳደሩ አገልግሎቱ ከተጀመረ ጊዜ አንስቶ አዳጊ ለውጦች መታየታቸውን ተናግረዋል።

‎ባለፈው በጀት ዓመት ከ50 ሚሊዮን ብር በላይ ተሰብስቦ ከ100 ሺህ በላይ ተጠቃሚዎች የሕክምና አገልግሎት እንዳገኙ ገልጸዋል።

‎አገልግሎቱ መታከም ለሚገባቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች ሙሉ በሙሉ ተደራሽ ባለመደረጉ ይህንን ታሳቢ ያደረገ ሥራ መሥራት ይጠይቃል ነው ያሉት።

‎የጤና መድኅን ተግባር ሰው ተኮር የኾነው የመረዳዳት ባህሪ የሚገለጽበት ነው ብለዋል። ለጤናው ሴክተር ፋይናንስን ከረጅዎች ለመላቀቅ ጤና መድኅን ላይ በሰፊው መሥራት እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል።

‎በየደረጃው ያሉ መሪዎች በቁርጠኝነት በመሥራት ተግባሩን ውጤታማ እንዲያደርጉ አሳስበዋል።

‎በዛሬው ዕለት የከተማ አሥተዳደሩ ጤና መምሪያ በፋሲሎ ክፍለ ከተማ የከነማ መድኃኒት ቤት አገልግሎት አስጀምሯል። የክልሉ ጤና ቢሮም ዘመናዊ አምቡላንስ መኪና ለከተማ አሥተዳደሩ አስረክቧል።

ለተደረገው ድጋፍ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

‎ዘጋቢ፦ ፍሬሕይዎት አዘዘው

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Previous articleዘምዘም ባንክ አክሲዮን ማኅበር ከታክስ በፊት ከ1 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በላይ ትርፍ ማስመዝገቡን አስታወቀ።
Next articleየሕዝብን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ ነው።