
ወልድያ: ታኅሣሥ 04/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የዞኑ ሴቶች፣ ወጣቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ መምሪያ የሴቶች ጥቃትን መከላከል ላይ ያተኮረ ምክክር ከባለድርሻ አካላት ጋር አካሂዷል።
የመምሪያው ኀላፊ እመቤት ደሳለኝ በ2018 በጀት ዓመት ብቻ 189 ሴቶች ጥቃት ደርሶባቸዋል ነው ያሉት።
ከእነዚህ ውስጥ 52 ሴቶች ከ18 ዓመት በታች መኾናቸውን ገልጸዋል።
በክልሉ ያለው ወቅታዊ የፀጥታ ችግር ለሴቶች ጥቃት መባባስ ምክንያት ነው ያሉት ኀላፊዋ ወደ ተቋማት መጥተው ያላሳወቁ ሌሎች ተጎጂዎችም ሊኖሩ ይችላሉ ነው ያሉት።
ተጎጂዎች ወልዲያ፣ ላሊበላ እና መቄት በሚገኙ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ተቋማት ሁሉን አቀፍ ድጋፍ እየተደረገላቸው መኾኑን ተናግረዋል።
የሴቶች ጥቃት የማኅበረሰብ ጥቃት ነው፤ የማኅበረሰብን ደኅንነት ዋስትና ያሳጣል ያሉት ኀላፊዋ የማኅበረሰብን ደኅንነት ለመጠበቅ የሴቶችን ጥቃት በትብብር መከላከል እንደሚገባ አሳስበዋል።
የምክክር ተሳታፊ ባለድርሻ አካላት የወልዲያ ከተማን አንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ጎብኝተዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
