
ጎንደር: ታኅሣሥ 02/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የጎንደር ከተማ አሥተዳደር እና ማዕከላዊ ጎንደር ዞን የሦስተኛ ዙር መካከለኛ እና ጀማሪ መሪ ሠልጣኞች በጎንደር ከተማ እየተሠሩ ያሉ የልማት ተግባራትን ተመልክተዋል።
ጀማሪ እና መካከለኛ መሪዎቹ አምራች የኢንዱስትሪ መንደሮችን፣ የሌማት ትሩፋት ሥራዎችን፣ የጎንደር
አብያተ መንግሥታት እድሳትን እና ሁለተኛ ዙር የኮሪደር ልማት ሥራዎችን ነው የጎበኙት።
የግብርና ምርት እና ምርታማነትን ማሳደግ፣ የቱሪዝም ሃብትን በመለየት ጥቅም ላይ ማዋል፣ ኢንዱስትሪ
ልማት እና ከተማን በማስዋብ ሥራዎች ላይ ለመሪዎቹ ሥልጠና መሰጠቱን የተናገሩት በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የጎንደር ከተማ አሥተዳደር ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት መምሪያ ኀላፊ ግርማይ ልጃለም ናቸው።
የጉብኝቱ መደረግ በሥልጠና ያገኙትን እውቀት በተጨባጭ መሬት ላይ እየተሠሩ ያሉ ተግባራትን አይተው ለሌሎችም እንዲያስተዋውቁ ዕድል የሚፈጥር ነው ብለዋል።
በሌማት ትሩፋት እና በኮሪደር ልማት ያዩትን ተሞክሮ በመውሰድ በየከተማቸው እና አካባቢያቸው ላይ እንዲሠሩ ዕድል ለመፍጠር ያለመ መኾኑን ኀላፊው ጠቅሰዋል።
ሥልጠናው መሪዎች ብልሹ አሠራርን በማስወገድ ዜጎች የሚፈልጉትን መልካም አሥተዳደር እንዲያሰፍኑ የሚያግዝ መኾኑን የተናገሩት ደግሞ የዞብል ክፍለ ከተማ ሴቶች ክንፍ ኀላፊ ወይዘሪት ሳምራዊት ውዱ ናቸው።
ሌላኛው የጉብኝቱ ተሳታፊ የጭልጋ ወረዳ ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኀላፊ መኳንንት ታረቀኝ የልማት ሥራዎቹ ዜጎች የሚጠይቁትን የመልማት ጥያቄዎች እየመለሱ ነው ብለዋል።
መሪዎች እነዚህን የልማት ሥራዎች ከዳር እንዲደርሱ የሚያደርገው እገዛ ልምድ የሚቀሰምበት እንደኾነ አንስተዋል።
በሌሎች የወረዳ ከተሞች ለሚጀመሩ የከተማ ማስዋብ እና ዜጎችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ሥራዎች ጥሩ ተሞክሮ የሚወሰድበት መኾኑን የገለጹት ደግሞ የአለፋ ወረዳ መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ኀላፊ ዋሴሁን ሞላ ናቸው።
እነዚህን የልማት ሥራዎች ወደ አካባቢያቸው ለማስፋት ጥሩ ልምድ የተገኘበት መኾኑንም ገልጸዋል።
ዘጋቢ:- ዳንኤል ወርቄ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
