ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ መጠናቀቅ የአፍሪካ ቀንድን የበለጠ እንደሚያስተሳስር ኬንያውያን ምሁራን ገለፁ።

150
ባሕር ዳር፡ ሰኔ 16/2012 ዓ.ም (አብመድ) ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለቀጣናዊ ትብብር አስፈላጊ መሆኑን ኬንያውያን ምሁራን አስታውቀዋል፡፡
 
“ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለቀጣናዊ ልማት እና ውህደት ያለው ጠቀሜታ” በሚል ርዕስ በናይሮቢ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ጋር በመተባበር ውይይት ተካሂዷል፡፡
 
በውይይቱ የተሳተፉ ኬንያውያን ምሁራንም ኢትዮጵያውያን የማንንም ፈቃድ እና ችሮታ ሳያስፈልጋቸው የራሳቸውን የተፈጥሮ ሀብት የማልማት መብት እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡ በቅኝ ግዛት ዘመን የተፈረሙ ስምምነቶች ተቀባይነት የሌላቸው እና ኋላ ቀር ሰነዶች መሆናቸውንም ምሁራኑ ማስረዳታቸውን በኬንያ የኢትዮጵያ ኤምባሲ አስታውቋል፡፡
 
የቅኝ ግዛት ዘመን ስምምነት ማንኛውም ሀገር የሚቀበለው አለመሆኑንም ነው የተናገሩት፡፡ በመሆኑም በሕዳሴ ግድቡ ጉዳይ የቀጣናው ሀገራት ሕዝቦች ከአትዮጵያውያን ጋር መሆናቸውንና ኢትዮጵያ ብቻዋን አለመሆኗን አረጋግጠዋል፡፡
 
በውይይቱ በናይሮቢ ዪኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ምሁራን፣ የቀድሞ የኬንያ ከፍተኛ የመንግስት ሥራ ኃላፊዎችና እና የቀጣናዊ ውህደት እና ልማት ጉዳዮች ተንታኝ አህመድ ሃሺ ተሳትፈዋል።
Previous articleአካል ጉዳተኛው የአምስት ዓመት ታዳጊ አካል ጉዳተኞችን ለማገዝ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ፓውንድ ድጋፍ አሰባሰበ፡፡
Next articleበኢትዮጵያ ተጨማሪ 185 ሰዎች የኮሮናቫይረስ ተገኘባቸው፡፡