
ባሕር ዳር: ኅዳር 23/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የሰሜን ጎጃም ዞን ግብርና መምሪያ “ጉዞ ወደ ሜካናይዜሽን” በሚል እሳቤ የግብርና ሜካናይዜሽን የንቅናቄ መድረክን እያካሄደ ነው፡፡
በመድረኩ ከሁሉም ወረዳዎች የመጡ ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎች፣ ሞዴል አርሶ አደሮች እና የኅብረት ሥራ ዩኒዬኖች ተገኝተዋል።
የሰሜን ጎጃም ዞን ምክትል አሥተዳዳሪ እና የግብርና መምሪያ ኀላፊ በለጠ ጥጋቡ የሰሜን ጎጃም ዞን እምቅ የግብርና አቅም ያለው እና ከ315 ሺህ ሄክታር በላይ በመኸር የሚታረስ መሬት ያለበት ዞን ነው ብለዋል።
ለብዙ ሺህ ዓመታት በበሬ ሲታረስ ኖሯል፤ ይህም በግብርናው እድገት ላይ ተጽዕኖ አሳድሮበታል ነው ያሉት። የግብርና ሥራው ከእርሻ እስከ ጉርሻ ድረስ በበሬ ጫንቃ የተንጠለጠለ ኾኖ ቆይቷል ነው ያሉት።
በዚህ ዘመን ታሪኩን በመቀየር የእርሻ ሥራ እስከ ምርት ስብሰባው ድረስ ዘመናዊ መሣሪያዎችን በመጠቀም ግብርናን ማዘመን እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።
መዋቅራዊ ሽግግር የማይቀር ነው ያሉት ምክትል አሥተዳዳሪው ግብርናው አምርቶ ለኢንዱስትሪው ያስረክባል ብለዋል። ስለዚህ ግብርናው ካልዘመነ መዋቅራዊ ሽግግር አይሳካም ነው ያሉት።
በዞኑ 100 ትራክተሮችን እና 50 ኮምባይነር ለማሠራጨት በዕቅድ የተያዘ ቢኾንም እስካሁን ከፍላጎት ባለፈ የተሠራ ሥራ አለመኖሩን ተናግረዋል።
የመድረኩ አስፈላጊነትም ፈጻሚው፣ አርሶ አደሮች እና ኅብረት ሥራ ማኅበራት በጋራ ኾነው ሜካናይዝድ የኾኑ የግብርና መሣሪያዎችን ለአርሶ አደሮች እንዲያቀርቡ ለማስቻል እና እንዲጠቀሙ ለማድረግ ነው ብለዋል።
የመድረኩ ተሳታፊዎች በወረዳ ቢያንስ ሦስት ትራክተር እንዲገዛ ማድረግ ተገቢ እንደኾነ አንስተዋል።
እንደ ዞን ሰብል በኮምባይነር የሚሰበሰብ ቢኾንም ኮምባይነሮቹ ከሌላ ክልል የሚመጡ በመኾናቸው እና በዞኑ ያለውን አቅም ተጠቅሞ ማሽኖችን ማቅረብ አስፈላጊ መኾኑንም ገልጸዋል።
ዘጋቢ፦ ፍሬሕይዎት አዘዘው
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
