
አዲስ አበባ: ኅዳር 09/2018 ዓ.ም (አሚኮ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በስልጤ ዞን የምሥራቅ ስልጤ ወረዳ አሥተዳዳሪ እና የግብርና ጽሕፈት ቤት ኀላፊ ሳሎ ፋኔ ወረዳው ከዚህ ቀደም በባሕር ዛፍ ምርት ይታወቅ እንደነበር ገልጸዋል።
ባለፉት አራት ዓመታት ግን የወረዳውን አቅም በመጠቀም በዓመት እስከ አራት ዙር ድረስ ምርት መስጠት ወደሚያስችል የሙዝ ተክል የመቀየር ሥራ ተሠርቷል ብለዋል።
በዚህም የአዋጭነት ጥናት ተጠንቶ ለአርሶ አደሮች ግንዛቤ በመፍጠር ምርት እና ምርታማነታቸው እንዲጨምር ማድረግ ተችሏል ነው ያሉት።
የአካባቢው አርሶ አደሮችም በሙዝ ክላስተር ልማት ከተሰማሩ በኋላ የገበያ ትስስር እየተፈጠረላቸው ተጠቃሚ መኾን መቻላቸውን ተናግረዋል። ከሙዝ ተክል ችግኝ ሽያጭም ተጠቃሚ መኾናቸውን ገልጸዋል።
የወረዳው አሥተዳዳሪ አካባቢው ለፍራፍሬ እና አትክልት ምርት አመቺ በመኾኑ አርሶ አደሮች በአቮካዶ፣ ስኳርድንች፣ ፓፓያ፣ ቡና እና ሌሎች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ምርቶች አምርተው ወደ ገበያ እንዲያቀርቡ በማድረግ የኢኮኖሚ ተጠቃሚ እንዲኾኑ ማድረግ ተችሏል ብለዋል።
በወረዳው አሁን ላይ የለውን 30 ሄክታር መሬት የሙዝ ተክል ሽፋን ወደ 50 ለማድረስ እየተሠራ መኾኑም ተመላክቷል።
ዘጋቢ፦ ቤተልሄም ሰለሞን
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
