
ባሕርዳር፡ ኅዳር 09/2018ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ብሔራዊ ክልል ምክር ቤት የበጀት እና ፋይናንስ ጉዳየች ቋሚ ኮሚቴ በቅርቡ ባረቀቀው አዲስ የገቢ ግብር አዋጅ ዙርያ ውይይት እያካሄደ ነው።
ረቂቅ አዋጁ ለክልሉ ምክር ቤት ቀርቦ ከመጽደቁ በፊት ነው ከየተቋማት የተጋበዙ እንግዶች እና የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች በተገኙበት ውይይት እየተደረገበት የሚገኘው።
የአማራ ክልል ምክር ቤት ምክትል አፈጉባኤ አማረ ሰጤ ከዚህ በፊት የነበረው የገቢ ግብር አዋጅ ረጅም ጊዜ ሳይሻሻል መቆየቱን እና በየጊዜው አዋጆችን ማሻሻል እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል።
ዛሬ መሻሻል የሚገባቸው የገቢ ግብር አዋጅ፣ የቴምብር ቀረጥ ክፍያ፣ የኤክሳይዝ ታክስ፣ የገጠር መሬት መጠቀሚያ ክፍያ እና የግብርና ሥራ የገቢ ግብርን የተመለከቱ ረቂቅ አዋጆች ቀርበው ውይይት እንደሚካሄድባቸው ነው የጠቀሱት።
በክልሉ ተስፋ ሰጭ የልማት ሥራዎች ተጀምረዋል ያሉት ምክትል አፈ ጉባኤው የልማት ሥራዎችን እና ሌሎችንም ሥራዎች ለመሥራት ግብርን በወቅቱ እና በአግባቡ መሠብሠብ አስፈላጊ መኾኑንም ነው የገለጹት።
በውይይቱ የሚገኙ ሀሳቦችም ረቂቅ አዋጁን ለማዳበር በግብዓትነት ይውላሉ ብለዋል።
ዘጋቢ፦ ሮዛ የሻነህ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
