
ደብረ ማርቆስ: ጥቅምት 30/2018 ዓ.ም (አሚኮ) በከተማ አሥተዳደሩ የሚስተዋለውን የፀጥታ ችግር ለመቅረፍ በርካታ የፀጥታ አካላት ተሰማርተው የከተማዋ ሰላም ለማስጠበቅ እየሠሩ ይገኛሉ።
በከተማ አሥተዳደሩም ሰላምን ለማስፈን በሚደረገው ጥረት የተሻለ አፈፃፀም ላስመዘገቡ የፖሊስ እና የአድማ መከላከል አባላት እውቅና እና ሽልማት ተበርክቷል።
የደብረ ማርቆስ ከተማ አሥተዳደር ፖሊስ መምሪያ ኀላፊ ኮማንደር ቢምረው አሰፋ ለፀጥታ አባላት የትምህርት፣ የማዕረግ እና የሰርተፍኬት ሽልማት መሰጠቱን ተናግረዋል። ሽልማቱ ለቀጣይ ግዳጅ የተጣለባቸውን ኀላፊነት እንዲወጡ የሚያስችል ነው ብለዋል።
ከተማዋን ለነዋሪዎች ምቹ እና ሰላማዊ ለማድረግ የፀጥታ አካላት ላደረጉት አስተዋፅኦ ምስጋና ያቀረቡት የደብረ ማርቆስ ከተማ አሥተዳደር የከንቲባ ተወካይ መኮንን ሙሉአዳም ወደፊት የተጀመረውን ሰላምን የማስፈን ሂደት በተሻለ ለመፈጸም መሥራት እንደሚገባ አሳስበዋል።
በእውቅና እና ሽልማት ዝግጅቱ ላይ የተገኙት በሀገር መከላከያ ሠራዊት ከፍተኛ አዛዥ ብርጋዴር ጀኔራል ሶፍያ መሃመድ ሀገራዊ አንድነት ለመፍጠር ሕዝብ እና መንግሥት የጣለባችሁን ኀላፊነት በመወጣታችሁ ክብር ይገባችኋል ነው ያሉት።
ሰላምን ለማስፈን ኅብረተሰቡም ከፀጥታ አካላት ጎን ሊቆም እንደሚገባም መልዕክት አስተላልፈዋል።
እውቅና እና ሽልማት የተደረገላቸው የፀጥታ አባላት የተሰጣቸው እውቅና ለተሻለ ሥራ እንደሚያነሳሳቸው ገልጸዋል። ከማኅበረሰቡ ጋር በመቀናጀት ለከተማዋ ሰላም መረጋገጥ ከመቸውም ጊዜ በላይ በትጋት እንደሚሠሩ አስገንዝበዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን
