
ባሕር ዳር: ጥቅምት 25/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የሳይበር ጥቃት ኾን ተብሎ ያልተፈቀዱ የኮምፒውተር ሥርዓቶችን፣ መሠረተ ልማቶች እና ኔትዎርኮች ላይ አጥፊ ሶፍትዌሮችን በመጠቀም በሕገ ወጥ መንገድ ዳታዎችን መበዝበዝ እና አገልግሎት የማስተጓጎል ተግባር ነው።
የሳይበር ጥቃት ከቴክኖሎጅ መሥፋፋት ጋር እያደገ የመጣ፣ የሀገራትን ሉዓላዊነት አደጋ ላይ የሚጥል፣ ሰላም እና ደኅንነትን የሚነሳ ከአንዱ የዓለም ጫፍ ወደ ሌላኛው ጫፍ በቀላሉ የሚዳረስ አደገኛ ወንጀል ነው።
የሳይበር ጥቃትን ለመከላከል የሳይበር ደኅንነት ማስጠበቂያ አማራጮችን መጠቀም የግድ ይላል።
በኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አሥተዳደር (INSA) ዋና ዳይሬክተር የሕግ እና የፖሊሲ ጉዳዩች አማካሪ ፍቅረሥላሴ ጌታቸው እንዳብራሩት የሳይበር ደኅንነት በሳይበር ምኅዳሩ የሚያጋጥሙ የደኅንነት ተጋላጭነቶችን ለመከላከል የሚወሰዱ እርምጃዎችን፣ የአሠራር ሥርዓቶችን እና የሕግ ማዕቀፎችን ያጠቃልላል።
በኢትዮጵያም የሳይበር ደኅንነትን ለመጠበቅ የሚያስችሉ የሕግ ማዕቀፎች ተዘጋጅተው በሥራ ላይ መዋላቸውን ይናገራሉ። ከእነዚህም ውስጥ የኮምፒዩተር ወንጀል አዋጅ ቁጥር 958/2008 ዓ.ም አንዱ መኾኑን ገልጸዋል።
በአዋጁ እንደተቀመጠው የኮምፒዩተር ወንጀል ማለት በኮምፒዩተር ሥርዓት እና በኮምፒዩተር መረጃ ወይም ኔትዎርክ ላይ የሚፈጸም ወንጀልን ያጠቃልላል።
በቴክኖሎጅ ውጤቶች እና በኔትወርክ አማካይነት የኮምፒዩተር ዳታን ከመደበኛ አሠራሩ ውጭ ማበላሸት ማዛባት እና ማሠራጨት የኮምፒዩተር ወንጀል አካል እንደኾነም ነው አቶ ፍቅረስላሴ ያብራሩት።
የአንድን ሰው ወይም ተቋም ኮምፒዩተር ሳይፈቀድለት ማግኘት በሕግ የተከለከለ እና የሚያስጠይቅ መኾኑንም አስረድተዋል።
ኾነ ብሎ ያለፈቃድ ወይም ከተሰጠው ፈቃድ ውጪ የኮምፒዩተር ሥርዓት፣ የኮምፒዩተር ዳታ ወይም የኔትዎርክ ተደራሽነት በከፊልም ኾነ በሙሉ ማግኘት ወንጀል እንደኾነ አንስተዋል፡፡ የኮምፒዩተር ወንጀል ሲፈጸም ከቀላል እስከ ከባድ የወንጀል ተጠያቂነት እንደሚያስከትል በአዋጁ የተደነገገ መኾኑንም ነው አቶ ፍቅረሥላሴ የገለጹት።
በአዋጁ እንደተገለጸው፦
ኮምፒዩተሮችን በምስጢር መቆለፍ፣ ጠንካራ የይለፍ ቃል መጠቀም፣ ይለፍ ቃልን በየወቅቱ ማደስ፣ የስልክ እና የኮምፒዩተር መተግበሪያዎችን አፕዴት ማድረግ፣ ያልታወቁ ሊንኮችን አለመክፈት፣ የመረጃ መቅጃ ወይም ባክ አፕ መያዝ፣ አንቲቫይረስ መጠቀም የሳይበር ጥቃትን ለመከላከል የሚወሰዱ የጥንቃቄ መንገዶች መኾናቸውን አቶ ፍቅረሥላሴ አስረድተዋል።
ዘጋቢ:- አሰፋ ልጥገበው
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
            
		