በታዳጊ ሴቶች ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ለመከላከል ‎እየተሠራ ነው።

3

ባሕር ዳር: ጥቅምት 22/2018 ዓ.ም (አሚኮ) ‎‎የአማራ ክልል ሴቶች፣ ወጣቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ “የእኔን ለውጥ የምመራ ታዳጊ ሴት ልጅ ነኝ” በሚል መሪ መልዕክት ዓለም አቀፍ የታዳጊ ሴቶች ወይም የልጃገረዶች ቀን ክልላዊ የማጠቃለያ መድረክ እያካሄደ ነው።

‎በመድረኩ የአማራ ክልል ሴቶች፣ ወጣቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ምክትል ኀላፊ ዝና ጌታቸው ዓለም አቀፍ የታዳጊ ሴቶች ቀን በየዓመቱ ጥቅምት 11 ቀን ሲከበር መቆየቱንም ጠቁመዋል።

‎በኢትዮጵያም ለስምንተኛ ጊዜ “የእኔን ለውጥ የምመራ ታዳጊ ሴት ልጅ ነኝ” በሚል መሪ መልዕክት እስከ ቀበሌ ድረስ በየደረጃው በተለያዩ ሁነቶች ሲከበር መቆየቱን ገልጸዋል።

‎የበዓሉ መከበር ዓላማው ታዳጊ ሴቶች ራሳቸውን እንዲያበቁ፣ መሪነት እንዲለማመዱ እና የሚያጋጥሟቸውን ችግሮች ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እንዲፈቱ ለማስቻል ነው ብለዋል።

‎በክልሉ ታዳጊ ሴቶችን ከጎጅ ልማዳዊ ድርጊቶች ለመከላከል የጎጅ ልማዳዊ ድርጊቶች አስወጋጅ ኮሚቴ ጥምረት ተደራጅቶ እየተሠራ መኾኑን ገልጸዋል።

‎በክልሉ በታዳጊ ሴቶች ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ለመከላከል ከሚመለከታቸው አካላት ጋር የግንዛቤ ማስጨበጥ ሥራ ተሠርቷል ነው ያሉት። ችግሮች ሲከሰቱም ከፍትሕ አካላት ጋር በመኾን ምላሽ እየተሰጠ ነው ብለዋል።

‎በዓሉ የሚከበረው ታዳጊ ሴቶች በክበባት ተደራጅተው ለመብቶቻቸው እንዲታገሉ ለማስቻል መኾኑንም ገልጸዋል።

‎ከትምህርት ገበታ ውጭ የኾኑትን የመመለስ እና የኢኮኖሚ ችግር ያለባቸውን ወላጆቻቸው በገቢ ማስገኛ ሥራዎች እንዲሠማሩ እና ልጆች እንዲማሩ በርካታ ሥራዎች እንደተሠሩም ገልጸዋል።

‎በመድረኩ የተለያዩ የሴት አደረጃጀቶች መሪዎች፣ መምህራን እና ታዳጊ ሴቶች ተሳትፈዋል።

‎ዘጋቢ፦ ፍሬሕይዎት አዘዘው

የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation

ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!

Previous article“የሌላን ሀቅ አልነካችም፤ የማይገባትን አልጠየቀችም”
Next articleከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርት መተካት ሀገራዊ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ነው።