
ጎንደር፡ ጥቅምት 21/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የጎንደር ዩኒቨርሲቲ አዲስ የተመደቡ ተማሪዎችን እየተቀበለ ነው።
ተማሪ ሃብተማሪያም አስረስ ከአዲስ አበባ ከተማ ነው ወደ ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ለመማር የመጣው። ጎንደር ዩኒቨርሲቲን የመረጠው የተሻለ ትምህርት እንደሚሰጥ ባገኘው ግንዛቤ ተመሥርቶ እንደኾነ ተናግሯል። ለአካባቢው አዲስ ቢኾንም የግቢው ማኅበረሰብ አቀባበል እንዳስደሰተውም ገልጿል።
ሌሎች አዲስ ገቢ ተማሪዎችም የግቢው ማኅበረሰብ እንደ ቤተሰብ እንደተቀበላቸው አንስተዋል።በቀጣይ ግባቸውን ለማሳካት ጥረት እንደሚያደርጉም ተናግረዋል።
አዲስ ገቢ ተማሪዎችን ሲቀበል ያገኘነው የዩኒቨርሲቲው ነባር ተማሪ ፋኖስ ዘውዱ ለተማሪዎች መኪና በማዘጋጀት እየተቀበሉ መኾኑን ተናግሯል።
በቀጣይም አዲስ ገቢ ተማሪዎች ግቢውን እንዲላመዱ እና የቃል ኪዳን ቤተሰብ እንዲይዙ ለማድረግ እንደሚሠሩ ገልጸዋል።
የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች አገልግሎት ዲን ሃይማኖት በላይ (ዶ.ር) ተማሪዎችን ለመቀበል የተለያዩ ዝግጅቶች ሲከናወኑ መቆየታቸውን አንስተዋል። የጎንደር ዩኒቨርሲቲ በ2018 የትምህርት ዘመን ከ3 ሺህ 400 በላይ አዲስ ገቢ ተማሪዎችን መቀበሉን ገልጸዋል። ተማሪዎች ከትናንት ጀምሮ ወደ ግቢው መግባታቸውንም ጠቅሰዋል።
በቀጣይ ተማሪዎች በሚማሩት ትምህርት ዘርፍ ችግር ፈች እንዲኾኑ ዩኒቨርሲቲው በትኩረት እንደሚሠራም ገልጸዋል።
አዲስ ገቢ ተማሪዎች ውጤታማ ለመኾን ጥረት እንዲያደርጉም አሳስበዋል።
ዘጋቢ፦ ያየህ ፈንቴ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
