
ባሕር ዳር: ጥቅምት 17/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ትምህርት መምሪያ “አንድም ሕጻን በምግብ እጦት ምክንያት ከትምህርት ገበታው እንዳይለይ ኀላፊነታችንን እንወጣ” በሚል መሪ መልዕክት የተማሪዎች ምገባ የሃብት ማሠባሠቢያ የንቅናቄ መድረክ እያካሄደ ይገኛል።
በመድረኩም ላይ የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ምክትል ከንቲባ አስሜ ብርሌ፣ የባሕርዳር ከተማ የብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኀላፊ ሞላ ሁሴን፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የንግዱ ማኅበረሰብ፣ ባንኮች፣ ኢንተርፕራይዞች፣ በትምህርት እና በጤናው ዘርፍ የተሰማሩ ባለሃብቶች እንዲሁም የግል ትምህርት ቤቶች ተገኝተዋል።
የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ምክትል ከንቲባ አስሜ ብርሌ ተማሪዎች በአግባቡ ትምህርታቸውን እንዲጨብጡ፣ ሀገር እንዲገነቡ፣ ለሀገር ዋልታ እና ማገር እንዲኾኑ ከቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶች ጀምሮ መንከባከብ ይገባል ብለዋል።
በትምህርት ቤቶች የተጀመረው የተማሪ ምገባ ተደራሽነቱን እያሰፋ ውጤቱም በተግባር የሚገለጥ እንዲኾን የማኅበረሰቡ ተሳትፎ እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል።
ዘጋቢ፦ ሰመሀል ፍስሀ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!
