
ገንዳ ውኃ: ጥቅምት 07/2018 ዓ.ም (አሚኮ) በምዕራብ ጎንደር ዞን ገንዳ ውኃ ከተማ በዘላቂ ሰላም እና ልማት ዙሪያ ከተለያዩ ወረዳዎች እና ከከተማ አሥተዳደሩ የተወጣጡ የኅብረሰተብ ክፍሎች ከክልሉ ከፍተኛ መሪዎች ጋር ውይይት አካሄደዋል።
የውይይቱ ተሳታፊዎች ዞኑ በማዕድን፣ በቱሪዝም እና በሰብል ልማት በርከት ያሉ ፀጋዎች እንዳሉት አንስተዋል።
እነዚህ ሃብቶች በተገቢው መንገድ ለመጠቀም ክልሉ እንዲያግዝም ጠይቀዋል።
በተለይ አየር መንገድ፣ ኢንዱስትሪ ፓርኮች እና መሰል የልማት ሥራዎች ሊገነቡ እንደሚገባ ነዋሪዎቹ ጠይቀዋል።
በመድረኩ የተገኙት በምክትል ርእሰ መሥተዳደር ማዕረግ የከተማ ዘርፍ አሥተባባሪ እና የከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ ኀላፊ አህመዲን መሐመድ (ዶ.ር) የነጭ ወርቅ ምድር የኾነው ምዕራብ ጎንደር ዞን የብዝኀ ሃብት ባለቤት ነው ብለዋል።
ዞኑ በርከት ያሉ የቱሪዝም፣ ባሕል እና ታሪክ ባለቤት ነው ያሉት ኀላፊው እነዚህን ያልተነኩ ፀጋዎች አጉልቶ ማውጣት እንደሚያስፈልግ አንስተው መንግሥት የአካባቢውን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ እንደሚሠራ አስረድተዋል።
ዞኑ ለኢንቨስትመንት የተመቸ አካባቢ በመኾኑ ባለሀብቶች በዘርፉ እንዲሰማሩ ጥሪ አቅርበዋል።
ከአየር መንገድ ግንባታ ጋር ተያይዞ በማኅበረሰቡ የሚነሳውን ጥያቄ ለመቅረፍም የክልሉ መንግሥት ለኢትዮጵያ አየር መንገድ ደብዳቤ ስለመጻፉ አስታውቀዋል።
ይህንንም ተከታትሎ ለማስፈጸም በትኩረት እንደሚሠራም አንስተዋል።
ዘጋቢ ፡- አዲስ ዓለማየሁ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን