
ደብረማርቆስ: መስከረም 30/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የሦሥተኛ ዙር የተቀናጀ የፖሊዮ ክትባት ዘመቻ መሰጠት መጀመሩን የሞጣ ከተማ አሥተዳደር ጤና ጽሕፈት ቤት አስታውቋል።
የሞጣ ከተማ አሥተዳደር ጤና ጽሕፈት ቤት ኀላፊ አየለ ገረመው በሦሥተኛው ዙር የተቀናጀ የፖሊዮ ክትባት ዘመቻ ዕድሜያቸው ከ10 ዓመት በታች ለኾኑ ሕጻናት ከመስከረም 30/2018 ዓ.ም እስከ ጥቅምት 03/2018 ዓ.ም ለተከታታይ አራት ቀናት በጤና ባለሙያዎች ቤት ለቤት ክትባቱ እንደሚሰጥ ተናግረዋል።
ዘመቻው በመደበኛው የክትባት መርሐ ግብር ያቋረጡ ዕድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች የኾኑ ሕጻናትን በመለየት በጤና ተቋማት፣ በትምህርት ቤት እና በጊዜያዊ የክትባት መስጫ ጣቢያ እንዲከተቡ የሚያስችል መኾኑን ተናግረዋል።
በከተማው በስድስቱም ቀበሌዎች፣ በትምህርት ቤቶች እና በጊዜያዊ የክትባት መስጫ ጣቢያዎች ውስጥ ክትባቱ መሰጠት መጀመሩን ገልጸዋል። ዕድሜአቸው ከ10 ዓመት በታች የኾኑ ሁሉም ሕጻናት ክትባቱን መውሰድ አለባቸው ብለዋል።
ከ17 ሺህ በላይ ሕጻናት በክትባቱ ተደራሽ ለማድረግ እየተሠራ መኾኑን ተናግረዋል። ኅብረተሰቡ የጤና ባለሙያዎች ቤት ለቤት ሲመጡ ልጆቹን በማስከተብ ኀላፊነቱን እንዲወጣም ጥሪ አቅርበዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!