
ባሕር ዳር: መስከረም 24/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ እያከናወናቸው በሚገኙ የሪፎርም ሥራዎች ዙሪያ መግለጫ ሰጥቷል።
በጠቅላይ መምሪው የሚዲያ እና ኮሙዩኒኬሽን ኀላፊ ረዳት ኮሚሽነር ክንዱ ወንዴ የኅብረተሰቡን ሰላም እና ደኅንነት ለማረጋገጥ፣ የአገልግሎት አሰጣጡን ለማቀላጠፍ እና አሠራሩን ለማዘመን ጠቅላይ መምሪያው የሪፎርም እና የዲጅታላይዜሽን ሥራዎችን እያከናወነ መኾኑን ገልጸዋል።
እየተተገበሩ የሚገኙት የሪፎርም ሥራዎች እና የቴክኖሎጅ ውጤቶች ወንጀልን በሠለጠነ መንገድ ለመከላከል ምቹ ኹኔታ የሚፈጥር ነው ብለዋል።
የምርመራ ሥራውን በተቀላጠፈ እና በጥራት ለማከናወን፣ የተጠርጣሪዎችን ሰብዓዊ መብት በጠበቀ መንገድ ለመተግበር አቅም የሚፈጥር እንደኾነም ነው የገለጹት።
ሠራተኛው የተጣለበትን ኀላፊነት በተገቢው መንገድ ማከናወን የሚያስችል ምቹ አካባቢን የፈጠረ መኾኑን ነው የተናገሩት።
የሪፎርም ሥራው በክልል ደረጃ ታጥሮ የሚቀር ሳይኾን እስከ ቀበሌ ድረስ የሚዘረጋ ይኾናል ብለዋል። ከዚህ ባለፈ በሥራ ላይ የአካል ጉዳት ሊያጋጥማቸው የሚችሉ አባሎች የተለያዩ ድጋፍ የሚያገኙበት አሠራር ላይ ትኩረት መደረጉንም ገልጸዋል።
የሪፎርም ሥራ ከዘመኑ ጋር የሚያድግ በመኾኑ ሁሉም የክልሉ የፖሊስ አባላት የሚተገበሩ የቴክኖሎጅ ውጤቶችን ፈጥኖ በመላመድ ነጻ እና ገለልተኛ ኾኖ የተጣለበትን የሕዝብ አደራ እንዲወጣ አሳስበዋል።
ክልሉ ያጋጠመውን የጸጥታ ችግር ወደ ቀደመ ሰላሙ ለመመለስ የክልሉ የጸጥታ መዋቅር ከፌዴራል የጸጥታ መዋቅር ጋር በመቀናጀት እየተሠራ መኾኑንም ገልጸዋል።
ዘጋቢ፦ ዳግማዊ ተሠራ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!