
ጎንደር: መስከረም 07/2018 ዓ.ም (አሚኮ) የነገ ተስፋ የተቀናጀ የልማት በጎ አድራጎት ድርጅት በጎንደር ከተማ ለሚገኙ ትምህርት ቤቶች የመማሪያ ቁሳቁስ ድጋፍ አድርጓል።
የነገ ተስፋ የተቀናጀ የልማት በጎ አድራጎት ድርጅት የፕሮግራም ማናጀር ዓለማየሁ ሙሉ በቸቸላ አንደኛ ደረጃ ሙሉ ሳይክል ትምህርት ቤት ተገኝተው ለ215 ተማሪዎች የደብተር እና እስክርቢቶ ድጋፍ አበርክተዋል።
ድጋፉ የተደረገላቸው የተማሪ ወላጆች የትምህርት ቁሳቁስ ለማሟላት በተቸገሩበት ወቅት የነገ ተስፋ የተቀናጀ የልማት በጎ አድራጎት ድርጅት ስላገዛቸው አመስግነዋል።
የጎንደር ከተማ አሥተዳደር ትምህርት መምሪያ ኀላፊ ስንታየሁ ነጋሽ በጎ አድራጊ ድርጅቶች የወላጆችን ሸክም ለማቅለል እየሠሩ መኾናቸውን ገልጸዋል። የተደረገው ድጋፍ ልጆች ትምህርታቸውን በተገቢው መልኩ እንዲከታተሉ ያደርጋል ነው ያሉት።
“የትምህርት ዘርፉን መደገፍ የነገ ተተኪ የሀገር ተስፋዎችን ማነጽ” በመኾኑ ማኅበረሰቡ እና ረጂ ድርጅቶች የበኩላቸውን እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።
የነገ ተስፋ የተቀናጀ የልማት በጎ አድራጎት ድርጅት በቀጣይም ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ የተደረገባቸውን የትምህርት ቁሳቁሶች በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኙ 2 ሺህ 500 ተማሪዎች ድጋፍ እንደሚያደርግ ተመላክቷል።
ዘጋቢ:- ተስፋዬ ጋሹ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!