የመንግሥትን የሰላም ጥሪ የተቀበሉ እና በጠዳ የሥልጠና ማዕከል የቆዩ ታጣቂዎች ሥልጠናቸውን አጠናቀቁ።

20
ጎንደር: ነሐሴ 29/2017 ዓ.ም (አሚኮ) ‎በአማራ ክልል ከተለያዩ አካባቢዎች በትጥቅ ትግል ውስጥ የነበሩ የቀድሞ ታጣቂዎች በጠዳ የሥልጠና ማዕከል ሲወስዱት የነበረውን ሥልጠና አጠናቅቀው ነው ዛሬ የተመረቁት።
‎በጠዳ የሥልጠና ማዕከል ሲሠለጥኑ የቆዩ ሠልጣኞች ለሰላም መስፈን የነበራቸውን ቁርጠኝነት በሥልጠናው ወቅት ማሳየታቸውን በማጠናቀቂያ መርሐ ግብሩ የአማራ ክልል ሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ምክትል ኀላፊ በሪሁን መንግሥቱ ገልጸዋል።
‎የብሔራዊ ተሃድሶ ኮሚሽን በሀገሪቱ በትጥቅ ትግል ላይ የሚገኙ ወገኖችን ወደ ማኅበረሰቡ እንዲቀላቀሉ በማድረግ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝም አቶ በሪሁን አንስተዋል።
‎የአማራ ክልል መንግሥት ሰላምን ለማረጋገጥ እየሠራ መኾኑን ያነሱት አቶ በሪሁን መንግሥቱ ለሰላም መስፈን ሁሉም ሊተባበር ይገባል ብለዋል።
‎የብሔራዊ ተሐድሶ ኮሚሽን በሀገሪቱ ሰላም እንዲረጋገጥ በትኩረት እየሠራ እንደሚገኝ የኮሚሽኑ የጠዳ ማዕከል አሥተባባሪ አቶ ግዛቸው መኩሪያ ተናግረዋል። ‎ሰላም እና ዴሞክራሲ እንዲሰፍን የብሔራዊ ተሐድሶ ኮሚሽን ኀላፊነቱን እየተወጣ ይገኛልም ብለዋል።
‎በስልጠናው የተገኙ ሀሳቦችን በግብዓትነት በመጠቀም ‎መንግሥትም፣ ኮሚሽኑም ይጠቀምባቸዋልም ብለዋል አቶ ግዛቸው። በጫካ የሚገኙ ወገኖች ለሰላም እጃቸውን እንዲዘረጉም ጥሪ አቅርበዋል።
‎ሰልጣኞች በበኩላቸው በሥልጠና ማዕከሉ ቆይታቸው በተሰጡ ሥልጠናዎች የአመለካከት ለውጥ ማምጣታቸውን አንስተዋል። ያገኙትን እውቀት በመጠቀም ሰላም እንዲሰፍን የሚጠበቅባቸውን ኀላፊነት እንደሚወጡም ተናግረዋል።
ዘጋቢ:- ‎ደስታ ካሳ
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን
Previous article“በምርት ዘመኑ ምርታማነትን በሄክታር 35 ኩንታል ለማድረስ እየተሠራ ይገኛል” ድረስ ሳህሉ (ዶ.ር)
Next articleለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚን መገንባት ይገባል።