
ደብረ ማርቆስ: ነሐሴ 15/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የምሥራቅ ጎጃም ዞን አሥተዳደር ጽሕፈት ቤት በ2017 በጀት ዓመት ከ44 ሺህ በላይ ሕጻናት የልደት ምዝገባ ማካሄዱን ገልጿል።
ሕጻናት ትክክለኛ እና ታማኝነት ያለው መረጃ እንዲኖራቸው መብታቸው እና ደኅንነታቸው እንዲጠበቅ የልደት ሰርተፍኬት ሊኖራቸው ይገባል።
የምሥራቅ ጎጃም ዞን አሥተዳደደር ጽሕፈት ቤት የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ አገልግሎት ቡድን መሪ አይተነው ወርቁ ሕጻናት መብታቸው እንዲጠበቅ እና ሕጋዊ ማስረጃ እንዲኖራቸው በወቅቱ መመዝገብ አለባቸው ብለዋል።
በዞኑ ከተወለዱበት ዕለት ጀምሮ እስከ አምስት ዓመት ዕድሜ የሚገኙ ሕጻናት ምዝገባ መካሄዳቸውን ተናግረዋል። በዞኑ የሕጻናትን ልደት ጨምሮ ሌሎች ኹነቶችንም መመዝገብ ተችሏል። በዚህም ከ72 ሺህ በላይ የኅብረተሰብ ክፍሎች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መኾናቸውን ገልጸዋል። ኅብረተሰቡም ከጊዜ ወደ ጊዜ የሲቪልና ቤተሰብ አገልግሎት ተጠቃሚ ለመኾን ግንዛቤው እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል።
ለፍትሕ እና አሥተዳደር፣ ለውጭ ጉዞ እና ሌሎች ማኅበራዊ ጉዳዮች የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ጠቀሜታ እንዳለውም ተናግረዋል።
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!