
ደብረማርቆስ፡ ነሐሴ 07/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን በማኅበራዊ ልማት ዘርፍ በተለይ በትምህርት ዘርፍ ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል።
የምሥራቅ ጎጃም ዞን ትምህርት መምሪያ ኀላፊ ጌታሁን ፈንቴ አሚኮ በትምህርት ተሳትፎ እና ተደራሽነትን በማሳደግ፣ ጥራት እንዲረጋገጥ፣ የትምህርት ተቋማት እንዲሻሻሉ እና ደረጃቸውን እንዲጠብቁ ውጤታማ ሥራ መሥራቱን ተናግረዋል።
በተማሪዎች እና በመምህራን እንዲሁም በማኅበረሰቡ ዘንድ ቀና መሥተጋብር እንዲፈጠር ድርሻውን የተወጣ ሚዲያ መኾኑንም ጠቁመዋል።
በትምህርት ዘርፍ ከቅድመ አንደኛ እሰከ ሁለተኛ ደረጃ ድረስ ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዲመጡ በማንቃት እንዲሁም የተግባር ተኮር የጎልማሶች ትምህርት ላይ ማኅበረሰቡን በማስገንዘብ ረገድ ሰፊ ሥራዎችን ሠርቷል ነው ያሉት።
የትምህርት ጥራት እንዲጠበቅ፣ በመደበኛ የመማር ማስተማር ሥራው ላይ የሚያጋጥሙ መሠረታዊ ችግሮችን በአጀንዳ ቀርጾ በተለያዩ ሚዲየሞቹ አድማጭ ተመልካቹን በማወያየት እና ለችግሮች መፍትሔ በማመላከት አሚኮ ድርሻውን ተወጥቷልም ብለዋል።
የትምህርት ተቋማት ገጽታቸው እንዲቀየር እና ደረጃቸውን እንዲጠብቁ በሀገር ውስጥ እና በውጭው ዓለም የሚገኙ ዜጎች የበኩላቸውን ሚና እንዲወጡ የማንቃት ሥራውን እንደሠራም ጠቁመዋል።
አሚኮ ከትምህርት ባሻገር በሁለንተናዊ ዘርፎች የዜጎችን ፍትሐዊ እና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ያረጋገጠ ተቋም እንደኾነም መምሪያ ኀላፊው ተናግረዋል።
በቀጣይም አሁን ካለበት ኀላፊነት በተጨማሪ ተደራሽነቱን በማስፋት እና የማኅበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ሊያረጋግጡ የሚችሉ ፕሮግራሞችን በመሥራት ሰፊውን አርሶ አደር እና የከተማ ነዋሪ ተደራሽ በማድረግ ሊሠራ ይገባልም ብለዋል።
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!