
አዲስ አበባ፡ ነሐሴ 05/2017 ዓ.ም (አሚኮ)የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን ተቋሙን ለሚቀላቀሉ አዲስ ሠልጣኝ ሠራተኞች አቀባበል አድርጓል።
ሠልጣኞቹ ከሁሉም የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች የተወጣጡ ናቸው። ሥልጠናውም የሚሰጠው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አስተባባሪነት እንደኾነ ተገልጿል።
የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታ በሠልጣኞቹ ላይ ትንሿን ኢትዮጵያ እንደሚያዩ ገልጸዋል። የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክትም አስተላልፈዋል።
“እናንተን እዚህ ለማድረስ ቤተሰቦቻችሁ፣ ሀገራችሁ እና እናንተ ብዙ ዋጋ ከፍላችኋል፤ የተከፈለው ዋጋ ፍሬ አፍርቶ እዚህ በመደረሳችሁ ለቤተሰቦቻችሁ፣ ለሀገራችሁ እና ለእናንተ ምሥጋና ይገባል፤ ይህን ዕድል በአግባቡ ተጠቀሙበት” ነው ያሉት በመልዕክታቸው።
በቀጣይ የሥራ ሕይወታቸው ስኬታማ ለመኾን ጠንክረው እንዲሠሩም አሳስበዋል።
ሥራው በሥነ ምግባር የታነጸ እና የሚሰጥን ኀላፊነት መወጣት የሚጠይቅ መኾኑን ጠቁመዋል። ሠልጣኞቹም በዚሁ ቅኝት መጓዝ እንደሚጠበቅባቸውም አስገንዝበዋል።
ተቋሙ ያለበትን ግዙፍ ሀገራዊ ኀላፊነት ለመወጣት እየሠራ መኾኑንም ጠቁመዋል።
ሠልጣኞቹ ተቋሙን ሲቀላቀሉ ይህን ኀላፊነት ለመወጣት ራሳቸውን ዝግጁ ማድረግ እንዳለባቸውም ተናግረዋል።
ተቋሙ በሚሠጠው ሥልጠና 3ሺህ 329 ሠልጣኞች ተሳታፊ እንደሚኾኑ ተመላክቷል።
ዘጋቢ፦ ሰላማዊት ነጋ
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን!