
ባሕር ዳር: ሐምሌ 28/2017 ዓ.ም (አሚኮ) የአማራ ክልል ኀብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የ2017 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ እና የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ ትውውቅ መድረክ በባሕር ዳር ከተማ እያካሔደ ነው።
የአማራ ክልል ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር በላይ በዛብህ ተቋሙ በክልሉ ውስጥ ጤና እና ጤና ነክ መረጃዎችን በመሠብሠብ እና በመተንተን ጉልህ ሚና እየተጫወተ ነው ብለዋል። “የኅብረተሰብ ጤና ችግሮችን መቆጣጠር ላይ በትኩረት እየተሠራ እንደኾነም” ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ኀብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር መሳይ ኀይሉ (ዶ.ር) ተከስተው የነበሩ የኅብረተሰብ ጤና ችግሮችን በትብብር እና በቅንጅት በመሥራት መቆጣጠር ተችሏል ብለዋል።
ኤም ፖክስን ጨምሮ የተከሰቱ ወረርሽኞችን መከላከል ላይ የግንዛቤ ፈጠራ ሥራ በልዩ ትኩረት እንደተከናወነም ገልጸዋል።
በክልሉ የኅብረተሰቡ ጤና አደጋ የኾኑት ወባ፣ ኮሌራ እና ኤም ፖክስ ላይ አኹንም በትኩረት የሚሠራባቸው ችግሮች እንደኾኑም ተነስቷል።
በመድረኩ የኢትዮጵያ ኀብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የሥራ ኀላፊዎችን ጨምሮ የክልል እና የዞን ጤና መምሪያ መሪዎች ተገኝተዋል።
ዘጋቢ: ፍሬሕይወት አዘዘው
የአሚኮ ዲጂታል ሚዲያ ቤተሰብ ይሁኑ!
👇👇👇
https://linktr.ee/AmharaMediaCorporation
ለኅብረተሰብ ለውጥ እንተጋለን